Go to full page →

የእግዚአብሔርን መንፈስ ማሳዘን Amh2SM 378

ሰዎች እንደ ሕዝብም ሆነ በግለሰብ ደረጃ እግዚአብሔርን ካልተውት በስተቀር እሱ በፍጹም አይተዋቸውም፡፡ ከውጭ የሚነሳ ተቃውሞ ትዕዛዛቱን እየጠበቁ ያሉትን የእግዚአብሔርን ሕዝብ እምነት አያደበዝዘውም፡፡ ንጽህናን እና እውነትን ለመተግበር ችላ ማለት የእግዚአብሔርን መንፈስ ከማሳዘኑም በተጨማሪ እግዚአብሔር ሊባርካቸው በመካከላቸው ስላልሆነ ሕዝቡን ደካማ ያደርጋቸዋል፡፡ ውስጣዊ ብልሽት በኢየሩሳሌም ላይ እንዳደረገው ሁሉ በዚህ ሕዝብ ላይም የእግዚአብሔርን ነቀፌታ ያመጣባቸዋል፡፡ እነሆ ለሌሎች የሚሰብኩ ሰዎች ለሌሎች ሰብከው ለራሳቸው የተጣሉ እንዳይሆኑ የሚማጸኑ ድምፆች ይሰሙ፣ ልባዊ ጸሎቶች ይደረጉ፡፡ ወንድሞቼ ሆይ፣ ከፊታችን ያለው ምን እንደሆነ ስለማናውቅ ብቸኛው ደህንነታችን የዓለም ብርሃን የሆነውን መከተል ነው፡፡ በጥንቱ ዓለም ላይ፣ በሶዶምና ጎሞራ፣ እንዲሁም በጥንቷ ኢየሩሳሌም ላይ የእግዚአብሔርን ቁጣ ያመጡ ኃጢአቶች የእኛም ኃጢአቶች ካልሆኑ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር እና ለእኛ ይሰራል፡፡ Amh2SM 378.3

እጅግ አነስተኛ የሆነ የእግዚአብሔርን ሕግ መተላለፍ ተላላፊውን በደለኛ ከማድረጉም በላይ ከእውነተኛ ልቡ ንስሃ ካልገባ እና ኃጢአትን ካልተወ በስተቀር በእርግጠኝነት ከሃዲ ይሆናል፡፡ በተቻለ መጠን እንደ ሕዝብ የሞራል ብክለትንና እየተባባሱ የሚሄዱ ኃጢአቶችን ሰፈር እናጽዳ፡፡ የጽድቅን የግብረገብ ዓላማ ከፍ ከፍ እያደረግን ነን በሚል ሕዝብ ላይ ኃጢአት ሰልፍ እያደረገ ሳለ እግዚአብሔር ኃይሉን ለእኛ እንዲያነሳ እና ጽድቅ እንዳደረገ ሕዝብ እንዲያድነን እንዴት መጠበቅ እንችላለን? …እንደ ሕዝብ ራሳችንን በእምነቱ ውስጥ ካላቆየን እና በቃልና በጽሁፍ ብቻ የእግዚአብሔርን ሕግ መቀበል ሳይሆን ከትዕዛዛቱ አንዷን እንኳን አውቀን ሳንጥስ እያንዳንዷን ካልጠበቅን ድክመትና ጥፋት ይመጣብናል፡፡ ይህ በእያንዳንዱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መከናወን ያለበት ሥራ ነው፡፡ እያንዳንዱ ሰው ክርስቲያን መሆን አለበት፡፡ Amh2SM 379.1