Go to full page →

የክርስቶስን ጽድቅ መልበስ Amh2SM 380

ለእውነት በመታዘዝ ነፍሳቸውን የሚያነጹ ቅሬታዎች ከፈተናው ሂደት ብርታትን በመሰብሰብ ከቦአቸው ባለው ክህደት ውስጥ የቅድስናን ውበት ያሳያሉ፡፡ እነዚህን ሁሉ «በእጄ መዳፍ ቀርጬአቸዋለሁ» ይላል (ኢሳ. 49፡16)፡፡ ዘላለማዊ በሆነ እና በማይጠፋ ማስታወሻ ተይዘዋል፡፡ አሁን እምነት፣ ሕያው እምነት ያስፈልጋል፡፡ የኃጢአተኞችን ልብ ሰንጥቆ የሚገባ ሕያው ምስክርነት እንዲኖረን እንፈልጋለን፡፡ እጅግ ብዙ ስብከትና እጅግ ጥቂት አገልግሎት ይታያል፡፡ ቅዱስ የሆነ ቅብአት ያስፈልጋል፡፡ የእውነት መንፈስና ግለት እንሻለን፡፡ አብዛኞቹ አገልጋዮች በራሳቸው የባሕርይ ጉድለት በገሚስ ሽባ የሆኑ ናቸው፡፡ የሚለውጠው የእግዚአብሔር ኃይል ያስፈልጋቸዋል፡፡ Amh2SM 380.3

አዳም ከመውደቁ በፊት እግዚአብሔር ከእርሱ ይፈልግ የነበረው ለሕጉ ሙሉ በሙሉ እንዲታዘዝ ነበር፡፡ ያኔ እግዚአብሔር ከአዳም የፈለገውን ዓይነት ፍጹም መታዘዝን፣ እንከን የለሽ ጽድቅን፣ በዓይኑ ፊት ጉድለት የሌለበት ሆኖ መገኘትን ዛሬም ይፈልግብናል፡፡ ሕጉ የሚፈልገውን ሁሉ ማድረግ እንድንችል እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ የክርስቶስን ጽድቅ ወደ ዕለታዊው ተግባር ማምጣት የሚችል እምነት ከሌለን በስተቀር ይህን ማድረግ አንችልም፡፡ Amh2SM 380.4

ውድ ወንድሞች ሆይ፣ ጌታ እየመጣ ነው፡፡ ሀሳባችሁንና ራሳችሁን አንስታችሁ ሃሴት አድርጉ፡፡ አስደሳች የሆነ ዜናን የሚሰሙ፣ ኢየሱስን እንወደዋለን የሚሉ ሁሉ ሊነገር በማይቻል ደስታና ክብር እንደሚሞሉ ምነው ማሰብ በቻልን፡፡ ይህ እያንዳንዱን ነፍስ ማስፈንጠዝ ያለበት፣ በቤቶቻችን በተደጋጋሚ መነገር ያለበት እና በመንገድ ላይ ለምናገኛቸው ሰዎችም መነገር ያለበት አስደሳች ዜና ነው፡፡ ከዚህ የበለጠ ምን አስደሳች ዜና ለሌሎች ሊነገር ይችላል! ከሚያምኑትም ሆነ ከማያምኑት ጋር መከፋፋትና መጣላት እግዚአብሔር እንድንሰራ የሰጠን ሥራ አይደለም፡፡ Amh2SM 381.1

ክርስቶስ አዳኜ፣ መስዋዕቴ እና ስርየቴ ከሆነ በፍጹም አልጠፋም፡፡ በእርሱ በማመኔ የዘላለም ሕይወት አለኝ፡፡ እነሆ እውነትን የሚያምኑ ሁሉ ኢየሱስን እንደ ግል አዳኛቸው አድርገው ምነው ባመኑ፡፡ እያወራሁ ያለሁት በሥራ ስላልተደገፈ ርካሽ እምነት ሳይሆን ልባዊ ስለሆነ ህያው፣ ስለማያቋርጥ፣ በውስጣችን ስለሚኖር፣ የእግዚአብሔርን ልጅ ሥጋ ስለሚበላና ደሙን ስለሚጠጣ እምነት ነው፡፡ የእግዚአብሔርን ሕግ ስለተላለፈ ምህረትን የሚፈልግ ብቻ ሳይሆን ከእግዚአብሔር ፊት ወደሚወጣው የፀሐይ ብርሃን ከፍ የሚያደርግም ነው፡፡ ወደ ሰማይ የመግባት መብት ማግኘት ብቻ ሳይሆን የተትረፈረፈ መግባት እንዲሆንልንም ጭምር ነው፡፡ Amh2SM 381.2