Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    የእርኩሳን መናፍስት መሣሪያዎች

    የሚታየው ዓለም ከማይታየው ዓለም ጋር ያለው ግንኙነት፣ የእግዚአብሔር መላእክት አገልግሎትና የእርኩሳን መናፋስት መሣርያዎች፣በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በግልፅ የተቀመጡ ከመሆናቸውም በላይ ከሰው ልጆች ታሪክ ጋር በማይነጣጣል መልኩ የተገመዱ ናቸው፡፡ በአንድ በኩል የእርኩሳን መናፍስትን መኖር አስመልክቶ እያደገ የመጣ የመጠራጠር አዝማምያ ሲኖር፣ በሌላ በኩል ደግሞ «መዳንን ይወርሱ ዘንድ ስላላቸው ለማገዝ የሚላኩ የሚያገለግሉ» (ዕብ 1፡14) ቅዱሳን መላእክት በብዙዎች ዘንድ እንደ ሙት መንፈስ ይቆጠራሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረው ግን፣ ክፉና መልካም መላእክት ስለመኖራቸው ብቻ ሳይሆን፣ እኚህ መላእክት ከሙታን በድን የወጡ የሙት መንፈሶች አለመሆናቸውን በማያጠራጥር ማስረጃ ያቀርባል፡፡ ከሰው ፍጥረት በፊት መላእክት ነበሩ፤ ምክንያቱም የምድር መሠረት በተጣለ ጊዜ «የንጋት ኮከቦች በአንድነት ዘመሩ እንዲሁም የእግዚአብሔር መላእክት ሁሉ በደስታ ጮሁ፡፡» (እዮብ 38፡7) ከሰው ውድቀት በኋላ መላእክት የህይወትን ዛፍ እንዲጠብቁ ተልከው ነበር፡፡ ይህም የሆነው ሰው ከመሞቱ በፊት ነበር፡፡ መላእክት በተፈጥሮ ከሰዎች የሚበልጡ ናቸው፣ ምክንያቱም ዘማሪው ዳዊት «የሰው ልጅን ከመላእክት በጥቂት አሳነስኸው» ይላልና፡፡ (መዝ 8፡5)፡፡ታተ 13.1

    በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለ ሰማያዊ ፍጡራን፣ ስለ ቁጥራቸው ብዛት፣ ስለ ኃይልና ክብራቸው እንዲሁም ከእግዚአብሔር መንግስት ጋር ስላላቸው ቁርኝት (ዝምድና) እና ከመዋጀት ሥራ ጋር ስላላቸው ግንኙነት ጭምር ተጠቁመናል፡፡ «እግዚአብሔር ዙፋኑን በሰማይ አጽንቷል መንግስቱም ሁሉን ትገዛለች፡፡» ነብዩም «የብዙ መላእክት ድምፅ በዙፋኑ ዙሪያ ሰማሁ» ይላል፡፡ የቃሉን ድምፅ እየሰሙ ፈቃዱን የሚፈፅሙትን የሚያገለግሉ «ኀያላን መላእክት» በነገሥታት ንጉሥ ዙፋን ፊት ይገኛሉ፡፡ (መዝ 103፡19-21 ፤ ራዕይ 5፡11)፡፡ በነብዩ ዳንኤል የታዩ የሰማይ መልእክተኞች ሺህ ጊዜ ሺህ እና እልፍ አእላፋት ነበሩ፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ደግሞ «የማይቆጠሩ የሰማይ ማህበራት» ብሎ ይገልፃቸዋል፡፡ (ዳንኤል 7፡10 ፤ ዕብ 12፡22)፡፡ የእግዚአብሔር መልእክተኞች እንደመሆናቸውም «የመብረቅ ብልጭታን በሚመስል» ፍጥነትና በሚያስገርም ክብር ይበራሉ፡፡ በአዳኛችን መቃብር አጠገብ የታየው መልአክ መልኩ እንደ መብረቅ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ነበር፡፡ ጠባቂዎቹን ከፍርሃት የተነሳ እንዲንቀጠቀጡ አደረጋቸው «እንደ ሞቱም ሆኑ» (ማቴ 28፡3-4)፡፡ ትምክህተኛው አሦርያዊ እግዚአብሔርን በዘለፈና ባንቋሸሸ ጊዜ፣ እስራኤልንም ለማጥፋት ባስፈራራ ጊዜ፣ በዚያች ሌሊት የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ከአሦሪያውያን ጭፋራ መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ ሰው ገደለ፡፡ ከሰናክሬምም ሠራዊት ተዋጊዎች መሪዎችና አለቆች ሞቱ፡፡ ስለዚህ ንጉሡ በውርደት ወደ ገዛ አገሩ ተመለሰ፡፡ (2 ነገሥት 19፡35 ፤ 2 ዜና 32፡21)፡፡ታተ 13.2

    የምህረትን ተልዕኮ ይዘው መላእክት ወደ እግዚአብሔር ልጆች ይላካሉ፡፡ ወደ አብራሃም የበረከትን የተስፋ ቃል ይዘው፣ ወደ ሠዶም በሮች ፃዲቁን ሎጥ ከእሳት ጥፋት ለማትረፍ፣ ወደ ኤልያስ በረሀብና በድካም በምድረ በዳ ሊሞት በነበረ ጊዜ፣ ወደ ኤልሳዕ በጠላቶች ተከቦ በነበረበት ጊዜ በእሳት ፈረሶችና ሠረገሎች ወደተከበበች ትንሽ ከተማ፣ ወደ ዳንኤል እግዚአብሔርን በማያውቀው ንጉሥ ቤት ሆኖ መለኮታዊ ጥበብን በሚሻበት ጊዜ፣ ወይም የአንበሳ እራት እንዲሆን በተደረገ ጊዜ፣ ወደ ጴጥሮስ በሄሮድስ እስር ቤት እንዲሞት በተፈረደበት ጊዜ፣ በፊሊጲስዩስ ወደ ታሰሩ እስረኞች፣ ወደ ጳውሎስና ጓደኞቹ የባሕር ማዕበል በተነሳባቸው ምሽት፣ ወንጌልን እንዲቀበል የቆርነሊዮስን አዕምሮ ብሩህ ለማድረግ፣ ጴጥሮስ የመዳንን መልዕክት ይዞ ወደ አሕዛብ እንዲሄድ ለመላክ እነዚህንና እነዚህን የመሰሉ ተግባራትን በማከናወን ቅዱሳን መላእክት ለዘመናት ሁሉ የእግዚአብሔርን ወገኖች አገልግለዋል፡፡ታተ 13.3

    ለእያንዳንዱ የክርስቶስ ተከታይ ጠባቂ መላክ ተሹሞለታል፡፡ እነዚህ ሰማያዊ ጠባቂዎች ከሠይጣን ኃይል ለፃድቃን መከታ ናቸው፡፡ ሰይጣን እንኳን ይህን እውነታ በመገንዘብ «በውኑ ኢዮብ እግዚአብሔርን የሚፈራው እንዲያው በከንቱ ነው? እርሱን ቤቱንና ዙርያውን ያለውንም ነገር ሁሉ አንተ አላጠርከውምን?» ሲል መስክሯል፡፡ (ኢዮብ 1፡9-10)፡፡ እግዚአብሔር ሕዝቡን የሚጠብቅበት መንገድ በመዝሙረኛው ዳዊት አነጋገር እንዲህ ተብሎ ተቀምጧል፡- «እግዚአብሔርን በሚፈሩት ዙሪያ የእግዚአብሔር መልአክ ይሰፍራል ያድናቸዋልም፡፡» (መዝ 34፡7) በእርሱ ስለሚያምኑት መድኃኒታችን ሲናገር እንዲህ አለ «ከእነዚህ ታናናሾች መካከል አንዱን እንዳትንቁ ተጠንቀቁ እላችኋለሁና በሰማያት መላእክቶቻቸው በሰማያት ያለውን የአባቴን ፊት ሁል ጊዜ ያያሉ፡፡» (ማቴ 18፡10)፡፡ የእግዚአብሔርን ልጆች ለማገልገል የተሾሙት መላእክት በሁሉም ጊዜ ወደ እርሱ ፊት መቅረብ ይችላሉ፡፡ታተ 13.4

    ስለዚህ ለእግዚአብሔር ወገኖች፣ ለአታላዪ ኃይልና ለማያንቀላፋው ለጨለማው ልዑል ክፋት የተጋለጡ እንዲሁም ከክፉ ኃይላት ሁሉ ጋር ለሚታገሉት የማያቋርጥ የሰማይ መላእክቶች ጥበቃ ተረጋግጧል፡፡ ይህ የጥበቃ ዋስትና ሳያስፈልግ የተሰጠ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ለልጆቹ የፀጋና የጥበቃ የተስፋ ቃል የሠጠው ብርቱ የሆኑ የክፋት ሠራዊቶች ስለሚያጋጥሟቸው ነው፡፡ እነዚህ የክፋት ሠራዊት ቁጥራቸው የበዛ፣ ለክፋት ቆርጠው የተነሱ፣ የማይታክቱ፣ አደገኝነታቸውንና ኃይላቸውን አለማወቅ እንዲሁም አለመጠንቀቅ ሊጐዳ ስለሚችል ነው፡፡ታተ 13.5

    በመጀመርያ ሲፈጠሩ እነዚህ እርኩሳን መናፋስት ከኃጢአት የነፁ፣ በተፈጥሯቸው ኃያልና ክብራቸውም አሁን የእግዚአብሔር መልክተኞች ከሆኑት ቅዱሳን ፍጡራን ጋር እኩል ነበር፡፡ በኃጢአት በመውደቃቸው ግን የእግዚአብሔርን ክብር ለማዋረድና ለሰዎች ጥፋት በአንድነት አብረዋል፡፡ በአመፃ ከሰይጣን ጋር በመተባበራቸውና ከእርሱም ጋር ከሰማይ በመባረራቸው በቀጣይ ዘመናት ሁሉ ሰይጣን በመለኮታዊ ስልጣን ላይ ባነሳው ጦር ተባብረውታል፡፡ ስለ ስብሰባቸውና መንግስታቸው፣ ስለተለያዩ ስርአታቸው፣ ስለ እውቀታቸውና ስለ ውስብስብነታቸው እንዲሁም በሰው ልጆች ሰላምና ደስታ ላይ ስለሚቀይሱት የተንኮል ቅየሳቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተነግሮናል፡፡ታተ 14.1

    የብሉይ ኪዳን ታሪክ ስለ እርኩሳን መናፍስት መኖርና ስለ መሣርያቸው አልፎ አልፎ ይጠቅሳል፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት እርኩሳን መናፍስት ጉልህ በሆነ መልኩ ኃይላቸውን የገለፁት፣ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ በነበረበት ጊዜ ስለሆነ ነው፡፡ ክርስቶስ ለሰው ልጅ መዋጀት የተዘጋጀውን እቅድ ተረክቦ ለመፈፀም የመጣ ሲሆን ሰይጣን ደግሞ ዓለምን ለመግዛት ባለመብትነቱን ለማረጋገጥ ከምንም ጊዜ በላይ ቆርጦ የተጋበት ጊዜ ነበር፡፡ ከፍልስጤም (Palestine) ምድር በቀር ባሉት በሌሎች የዓለም ክፍሎችም ሁሉ የጣዖት አምልኮን ማስረፅ ችሏል፡፡ ክርስቶስ ደግሞ ለሰይጣን አገዛዝ እጇን ሙሉ በሙሉ ወዳልሰጠችው አገር ሕዝብ የሰማይን ብርሃን ለማብራት መጣ፡፡ በዚህ ቦታ ሁለት ተቀናቃኝ ኃይሎች የበላይነትንና የይገባኛል ጥያቄ አቀረቡ፤ ኢየሱስ እርሱን የሚሹትን በእርሱ ሰላምንና ይቅርታን ለማግኘት ይችሉ ዘንድ የፍቅር እጆቹን ዘርግቶ ይጠራቸውም ነበር፡፡ የጨለማ ሠራዊቶች ገደብ የሌለው ቁጥጥር እንደሌላቸው አይተው የክርስቶስ ተልዕኮ ከተሳካ ግዛታቸው በቅርብ እንደሚያበቃ አስተዋሉ፡፡ ሰይጣን በሰንሰለት እንደታሰረ አንበሳ ተቆጥቶ ግልፅ በሆነና በድፍረት በተሞላ ተቃውሞ በሰው ሥጋና ነፍስ ላይ ኃይሉን አሳየ፡፡ታተ 14.2

    በአዲስ ኪዳን ውስጥ በሰይጣን ተይዘው ስለነበሩ ሰዎች እውነታ በግልፅ ተጠቅሷል፡፡ እንዲህ ሲቸገሩ የነበሩ ሰዎች እንዲሁ በተፈጥሮ በሚመጣ ህመም ብቻ አልነበረም ሲሰቃዩ የነበሩት፡፡ ክርስቶስ ከምን ጋር እየታገለ እንደሆነ ፍፁም የሆነ ግንዛቤ ነበረው፤ የእርኩሳን መናፍስትን በእርግጥ መኖርና ሥራቸውን በትክክል አውቋል፡፡ታተ 14.3

    ስለ ቁጥራቸው ብዛት፣ ስለ ኃይላቸውና ስለ ጐጂነታቸው፣ እንዲሁም ስለ ክርስቶስ ኃይልና ምህረት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ክርስቶስ በጌርጌሳኖን በሳጥናኤል የተያዙትን ሰዎች የፈወሰበት የሚያስደንቅና ሊስተዋል የሚገባ ምሳሌ ተቀምጧል፡፡ እነዚያ በሰይጣን የተያዙ ምስኪን ጐስቋሎች እገዳን ሁሉ በመጣስ እየተቅበዘበዙ፣ ዓረፋን እየደፈቁ፣ በቁጣ እየገነፈሉ አየሩን በጩኸት ይሞሉት ነበር፡፡ እራሳቸውን ለመጉዳት ወደ እነርሱ ለመቅረብ የሞከሩትን ለአደጋ ያጋልጡ ነበር፡፡ታተ 14.4

    የሚደማውና ቅርፁን ያጣው ሰውነታቸው እንዲሁም የተቃወሰው አይምሯቸው ለጨለማው ልዑል አስደሳች ትዕይንት ነበር፡፡ በዚህ አካኋን የሚሠቃዩት ከተቆጣጣራቸው አንዱ እርኩስ መንፈስ «ስሜ ሌጊዎን ነው፣ ብዙ ነንና» ሲል ተናግሯል፡፡ (ማር 5፡9) በሮም ሠራዊቶች ውስጥ አንድ ሌጊዎን ከሦስት እስከ አምስት ሺህ ወታደሮችን ይወክላል፡፡ የሰይጣን ሠራዊቶችም በጦር መሪ የተከፋፈሉ ሲሆን እነዚህ እርኩሳን መናፍስት የተመደቡበት የጦር ክፍል በቁጥር ከሌጊዎን ያነሰ አልነበረም፡፡ታተ 14.5

    በኢየሱስ ትዕዛዝ፣ እርኩሳን መናፍስቱ የያዟቸውን ሰዎች ለቀዋቸው በፀጥታ፣ ራሳቸውን በማስገዛትና በእርጋታ በክርስቶስ እግር ስር ትተዋቸው ሄዱ፡፡ አጋንንቱ ግን የአሳማ መንጋን ይዘው ወደ ባሕር ይገቡ ዘንድ ተፈቀደላቸው፡፡ ለጌርጌሳኖን ነዋሪዎች ግን የአሳማዎቹ ጥፋት ክርስቶስ ከሠጠው በረከት በለጠባቸው፤ መለኮታዊ ፈዋሹንም ከዚያ ለቆ እንዲሄድ ተማፀኑት፡፡ ይህም ውጤት ሰይጣን አስቀድሞ ሊያሳካ የቀየሰው ቅየሳ ነበር፡፡ ስለ እጦታቸው ወቀሳውን በኢየሱስ ላይ እንዲጥሉ የሕዝቡን ፍርሐት በማነሳሳት የክርስቶስን ቃል እንዳይሰሙ አገዳቸው፡፡ ሰይጣን ነቀፋውን ሊሆን ወደሚገባው ወደ ራሱና ወደ ወኪሎቹ በማድረግ ፈንታ «ክርስቲያኖች የእጦት፣ የዕድለ ቢስነትና የስቃይ መንስኤዎች ናቸው» በማለት ዘወትር ይወነጅላል፡፡ታተ 14.6

    የክርስቶስ ዓላማዎች ግን አልተሰናከሉም፡፡ እርኩሳን መናፍስቱ አሳማዎቹን እንዲጠፉ የፈቀደላቸው ለትርፍ ሲሉ እነዚያን እርኩስ እንስሶች የሚያረቡትን አይሁዳውያን ለመገሠፅ ነበር፡፡ ክርስቶስ አጋንቶቹን ባይከለክል ኖሮ አሳማዎቹን ብቻ ሳይሆን እረኞቹንም፣ ባለቤቶቹንም ወደ ባሕር ውስጥ ያሰጥማቸው ነበር፡፡ ክርስቶስ ለምህረቱ የተጠቀመው ኃይሉ የእረኞቹና የጠባቂዎቹ መዳን ብቸኛ ምክንያቱ ሆኗል፡፡ ከዚህም በላይ ይህ ክስተት የተፈቀደው ሰይጣን በሰውም ሆነ በእንስሳ ላይ የሚያሳየውን የጭካኔ ኃይል ደቀ መዛሙርቱ አይተው ይመሰክሩ ዘንድ ነው፡፡ አዳኛችን ተከታዮቹ በሰይጣን እንዳይሳሳቱና ለተንኮሉም እንዳይሸነፉ የጠላታቸውን ምንነት ያውቁ ዘንድ የእርሱ ፍላጐት ነበር፡፡ በተጨማሪም የአካባቢው ሰዎች እርሱ የሰይጣንን ቀንበር ለመስበርና ምርኮኞቹን ለማስለቀቅ ኃይል ያለው መሆኑን ያዩ ዘንድ ፈቃዱ ነበር፡፡ እየሱስ እራሱ ከሥፍራው ለቆ የሄደ ቢሆንም በእርሱ ድንቅ ሥራ ነፃ የወጡት ሰዎች ግን የእርሱን ምህረትና ረድኤት ለመመስከር ቀርተዋል፡፡ታተ 14.7

    ሌሎች ተመሳሳይ ባህሪ ያላቸው ክስተቶች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተመዝግበዋል፡፡ ሰይጣን ክፉኛ ሲያሰቃያት ከነበረው ከሲሮፊኒቃዊትዋ ሴት ልጅ ኢየሱስ በቃሉ ጋኔኑን አስወጥቶላታል፡፡ (ማር 7፡26-30)፡፡ ያደረበት እርኩስ መንፈስ «ሊገድለው ፈልጐ ዘወትር እሳትና ውሃ ውስጥ ይጥለው የነበረው ወጣት» (ማር 9፡17-27) ሌላው ሊጠቀስ የሚችል ነው፡፡ «በእርኩስ ጋኔን መንፈስ» (ሉቃስ 4፡33-36) ሲሰቃይ የነበረውና በቅፍርናሆም የነበረውን ምኩራብ የሰንበት ፀጥታ ያወከው ሰው እነዚህ ሁሉ በሩህሩሁ አዳኝ ተፈውሰዋል፡፡ በአብዛኛው ገጠመኞቹ ክርስቶስ ጋኔንን እንደ አስተዋይ ፍጡር ሁሉ እየጠራው ተጠቂዎቹን ለቆ እንዲወጣና ከዚያም ወዲያ እንዳያሰቃያቸው ያዝ ነበር፡፡ በቅፍርናሆም የሚያመልኩም ይህን ታላቅ ኃይሉን በማየት «ሰዎችም ተገረሙ፣ እርስ በእርሳቸውም ለመሆኑ ይህ ትምህርት ምንድን ነው? በስልጣንና በኃይል ርኩሳን መናፍስትን ያዛል፣ እነርሱም እኮ ይወጣሉ ተባባሉ፡፡» (ሉቃስ 4፡36)፡፡ታተ 15.1

    በአጋንንት የተያዙ ሰዎች ብዙውን ጊዜ በታላቅ የመሰቃየት ሁኔታ ላይ እንዳሉ ተደርጐ ይቀርባል፡፡ ሆኖም አንዳንዶች በዚህ ሁኔታ ውጥስ አይጠቃለሉም፡፡ ልዩ የሆነ ኃይልን ለማግኘት ሲሉ አንዳንዶች በጥንቁልና መንፈስ የተያዙ እንደ ስሞን ባጐስ፣ እንደ ዓስማተኛው ኤሊሞስ እንዲሁም ጳውሎስንና ሲላስን በፊሊጵሲዮስ ከተማ ስትከተል የነበረችው ልጅ በዚህ ጐራ ይመደባሉ፡፡ታተ 15.2

    በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለ ሰይጣን መሳርያዎችና ስለ መላእክቶቹ መኖር ቀጥተኛ፣ ብዙና በቂ ምስክርነት እያለ፣ ይህን እውነታ ከሚክዱት በላይ ከእርኩሳን መናፍስት የተነሳ ለበለጠ አደጋ የሚጋለጥ ማንም የለም፡፡ የሰይጣንንና የእርኩሳን መናፍስትን መሳርያዎችና ማታለያዎችን እስካላወቁ ድረስ ከሚገመተው በላይ ተጠቂ ናቸው፡፡ ብዙዎች በራሳቸው ጥበብ አማካኝነት የተመሩ እየመሰላቸው ለሰይጣንና ለመላእክቶቹ አስተያየቶች ጆሯቸውን ሰጥተዋል፡፡ ከዚህም የተነሳ ወደ ዘመን ፍፃሜ በደረስን ቁጥርና ሰይጣንም ለማሳሳትና ለማጥፋት በበለጠ ኃይል በሚሰራበት ጊዜ «ሰይጣን የለም» የሚለው እምነት በየቦታው እንዲስፋፋ ያደርጋል፡፡ እራሱንና የሚሰራበትን መንገድ መሰወር (መደበቅ) የእርሱ መርሕ ነው፡፡ታተ 15.3

    ታላቁ አሳሳች እኛ የእርሱን ዘዴና እቅድ ከማወቃችን በላይ የሚያሰጋው ሌላ አንዳች ነገር የለውም፡፡ የራሱን እውነተኛ ባሕሪና ዓላማ ይበልጥ በመሰወር ከፌዝና ንቀት ያለፈ የጠነከረ ስሜት እንዳይቀሰቀስበት አድርጐ እራሱን ያቀርባል፡፡ አስቂኝ ወይም አፀያፊ ምስል ያለው፣ ቅርፁም የተበላሸ፣ ግማሽ ሰው-ግማሽ እንስሳ አድርገው ሲስሉት ደስ ይለዋል፡፡ እራሳቸውን እንደ አስተዋይና አዋቂ አድርገው በሚያስቡት ሰዎች ዘንድ ስሙ በስፖርት ቦታዎችና ቀልዶች በሚነገሩባቸው መድረኮች ሲነሳ መስማት ያስደስተዋል፡፡ታተ 15.4

    በእውነት እንደዚህ አይነት ፍጡር ይኖር ይሆን? ተብሎ በስፋት የሚጠየቀው ሰይጣን በፍፁም ጥበብ እራሱን በመደበቁ ነው፡፡ በግልፅ በተቀመጠው በመጽሐፍ ቅዱስ ምስክርነት ላይ የሚነዛው የሐሰት ንድፈ ሐሳብ በመላው ኃይማኖት ዓለም ተቀባይነት ማግኘቱ የሰይጣንን ስኬት የሚያስረዳ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ስለ አጥፊው ተግባሩ ብዙ ምሳሌዎችን እየሰጠ፣ የምስጢር ኃይሎቹን በፊታችን እያጋለጠ፣ ከጥቃቶቹም እራሳችንን እንድንጠብቅ የሚያስጠነቅቀን ሰይጣን ስለ ተፅእኖው የማያውቁትን ሰዎች አእምሮ ሳያመነታ በቀላሉ ስለሚቆጣጠር ነው፡፡ታተ 15.5

    ከሁሉም በላይ በሆነው በመድኃኒታችን ኃይል መጠለያና መድንን ማግኘት የማንችል ቢሆን ኑሮ፣ የሰይጣንና የሠራዊቱ ኃይል፣ ክፋትና ተንኮሉ ፍፁም ሊያሸብረን ይችል ነበር፡፡ ንብረታችንንና ሕይወታችንን ከክፉ ሰዎች ለመጠበቅ ቤታችንን በጥንቃቄ በመቀርቀርያና በቁልፍ እንጠብቃለን፡፡ ነገር ግን ወደ እኛ ለመድረስ ሳያቋርጡ ስለሚሹትና ጥቃታቸውንም በእራሳችን አቅም ለመከላከል ምንም ዓይነት ዘዴ ስለሌለን ስለ ክፉ መላእክት እምብዛም አናስብም፡፡ ቢፈቀድላቸው አእምሮአችንን ማዛባት፣ አካላችንን ማሳመምና ማሰቃየት፣ ንብረታችንንና ሕይወታችንንም ማጥፋት ይችላሉ፡፡ ብቸኛ የደስታ ምንጫቸው መከራና ጥፋት ነው፡፡ መለኮታዊ ፈቃድን በመቋቋማቸውና ለሰይጣን ፈተና እራሳቸውን አሳልፈው በመስጠታቸው ለእርኩሳን መናፍስት ቁጥጥር እግዚአብሔር አሳልፎ የሰጣቸው ሰዎች ሁኔታ እጅግ አስፈሪ ነው፡፡ ክርስቶስን የሚከተሉ ግን ሁሌም በእርሱ ጥበቃና ጥንቃቄ ስር ስለሆኑ ለአደጋ ያልተጋለጡ ናቸው፡፡ በጥንካሬ የሚያይሉ መላእክት እንዲጠብቋቸው ከሰማይ ይላካሉ፡፡ ሰይጣንም፣ እግዚአብሔር ለወገኖቹ ያቆመውን ጠባቂ ጥሶ ማለፍ አይችልም፡፡ታተ 15.6

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents