Go to full page →

28—ነፍስን መፈወስ CLAmh 154

ብዙ በጥፋታቸው በሽታ የሸመቱ ሰዎች ወደ ክርስቶስ ቢመጡም አልፈውሳችሁም ብሎ አልመለሳቸውም፡፡ የእርሱ ጽድቅ በእነርሱ ላይ ሲያበራ ኃጢአታቸውን ተገንዝበው ብዙዎቹ ከመንፈሳዊና ከስጋዊ ደዌያቸው ተፈወሱ፡፡ CLAmh 154.1

ከበሽተኞቹ መካከል አንድ የቅፍርናሆን ሽባ ነበር፡፡ በበሽታው የተለከፈው ሰው ኑሮው በተሳሳተ የኃጢአት መንገድ ስለተመራ ነበር፡፡ የሕሊና ወቀሳና ሕመሙ ያሰቃየው ነበር፡፡ ሐኪሞችንና ፈሪሣውያንን እንዲያክሙት ቢጠይቅም ፋይዳ አላገኘም፡፡ አትድንም ብለው ተስፋ አስቈረጡት፡፡ ኃጢአተኛ መሆኑን ለሕዝብ አስታወቁ፡፡ በእግዚአብሔር ቁጣም እንደሚሞት አስታውቀው ነበር፡፡ CLAmh 154.2

ሽባው ሰው ተስፋ ቆርጦ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ስለየሱስ ሰማ፡፡ ሌሎች እንደእርሱ ኃጢአተኞችና ተስፋ የቆረጡ መዳናቸውን ሲሰማ እርሱንም ወደ መድኅን ቢወስዱት እንደሚድን አመነ፡፡ የበሽታው መነሻ ትዝ ሲለው ተስፋው ይመነምንና ብቻ እድን ይሆናል ብሎ ያስብ ነበር፡፡ CLAmh 154.3

ከጉጉቱ የተነሣ የኃጢአቱን ክብደት ረሳ፡፡ የሱስን ለማየትና የመዳንን ጸጋ ተቀብሎ ሰላም ለማግኘት ቸኮለ፡፡ ከዚያ በኋላ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ቢሞትም ቢድንም አይጸጽተውም፡፡ CLAmh 154.4

የሚያባክነው ጊዜ አልነበረውም፤ የበሰበሰው ገላው ከሞት አፋፍ አድርሶት ነበር፡፡ ወዳጆቹ ወደ የሱስ ተሸክመው እንዲወስዱት ቢጠይቃቸው በደስታ ጥያቄውን ፈጸሙለት፡፡ ግን በቤቱ ውስጥና በቤቱ አካባቢ ያለው ሕዝብ ስለበዛ ወደ እርሱ መቅረብና ንግግሩን ማዳመጥ አስቸጋሪ ነበር፡፡ የሱስ በጴጥሮስ ቤት ውስጥ ያስተምር ነበር፡፡ ደቀመዛሙርቱ እንደ ልማዳቸው በአጠገቡ ተቀምጠው ነበር፡፡ “ከገሊላና ከይሁዳ መንደሮች ሁሉ ከየሩሳሌምም መጥተው የነበሩ ሁሉ ፈሪሣውያንና የሕግ መምህራን ሁሉ ተቀምጠው ነበር፡፡” (ሉቃስ 5፡17)፡፡ በጉባዔው ላይ ሕይወት ሰጭ መንፈስ ያንዣብብ ነበር፡፡ ፈሪሣውያን ግን ከበረከቱ አልተሳተፉም ነበር፡፡ ብዙዎቹም የሱስን ሊወነጅሉ የሚሞክሩ ሰላዮች ነበሩ፡፡ ከእነዚህ ሌላ በጉጉት፤ በአክብሮት፤ በቅንና በንጹህ ልቦና የቀረቡ ሰዎች በብዛት ነበሩ፡፡ የልዩ ልዩ አገር ሰዎች ልዩ ልዩ የኑሮ ደረጃ ያላቸው ሰዎች ነበሩ፡፡ “እርሱም እንዲፈውስ የጌታ ኃይል ሆነለት፡፡” (ሉቃስ 5፡17)፡፡ ግን የመዳንን ጸጋ ያልተቀበሉት ፈሪሣውያን በረከቱ አለፋቸው፡፡ “የተራቡትን በበጎ ነገር አጥግቦአል፤ ባለጠጎችንም ባዶአቸውን ሰዶአቸዋል፡፡” ሉቃስ 1፡53)፡፡ CLAmh 154.5