Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents
ሥነ - ትምህርት - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    «የተፃፉ ነገሮች ሁሉ ለእኛ ትምህርት ተፃፉ፡፡»

    ምዕራፍ 5—ለእስራኤል የተሰጠው ትምህርት

    «ጌታ ብቻ መራው፡፡»
    «እርሱ አስተማረው እንደ
    ዐይኑ ብሌን ጠበቀው፡፡«
    EDA 32.1

    በኤደን ገነት ውስጥ ይሰጥ የነበረው የትምህርት ሥርዓት ያተኮረው በቤተሰብ ውስጥ ነበር፡፡ «አዳም የእግዚአብሔር ልጅ ነበረ፡፡» ሉቃ 3፡38 የሁሉም የበላይ የሆነው አምላክ ልጆች መመሪያዎችን ያገሀኑ የነበረው ከአባታቸው ነበር፡፡ በእውነተኛው አባባል የእነሱ ትምህርት ቤት የቤተሰብ ትምህርት ቤት ነበር፡፡EDA 32.2

    ከሰው ልጅ ውድቀት በኋላ በፀደቀው፤ መለኮት ለትምህርት ባመጣው እቅድ ውስጥ ክርስቶስ የአባት ወኪል ሆኖ እግዚአብሔርንና ሰውን የሚያገናኝ ኃይል መሆኑ ተገልጾአል፡፡ ለሰው ልጅ ታላቁ መምህር እርሱ ነው፡፡ እርሱም ወንዶችና ሴቶች የርሱ ወኪል እንዲሆኑ ክህነት ሰጣቸው እናም ቤታቸው እንደትምህርት ቤት ወላጆች ደግሞ መምህራን ሆኑ፡EDA 32.3

    በቤተሰብ ላይ የተማከለው ትምህርት በሐዋሪያት ዘመን ሰፍኖ የነበረ ነው፡፡ በመሆኑም በዚያ ዘመን ለተቋቋሙት ትምህርት ቤቶች እግዚአብሔር ባሕሪይን ለማዳበር የሚያስችል እጅግ ምቹ ሁኔታን ፈጠረላቸው፡፡ በእርሱ መመሪያ ሥር የነበሩ ሰዎች እርሱ ቀድሞ በመጀመሪያ የመረጠውን የሕይወት እቅድ ፀንተው ተከተሉ፡፡ ከእግዚአብሔር ተለይተው የሄዱ ሰዎች ግን ለራሳቸው ከተሞችን ቆረቆሩ፡፡ በውስጣቸውም ተሰበሰቡ፡፡ በጌጣጌጥ አሸብርቀው፤ በምቾትና ደካማ ሥጋዌ ምኞት የዛሬዎቹን የዓለም ከተሞች ባረከሰው እርግማን ተኩራሩ፡፡ እግዚአብሔር ለሕይወት ያስቀመጣቸውን መሠረታዊ ሀሳቦች አጥብቀው የያዙ ሰዎች ግን በሜዳዎችና በየኮረብታዎች ላይ ሰፈሩ፡፡ እነሱም የከብትና የበግን መንጋ በመጠበቅና መሬትን ለማረስ የሚተዳደሩ ነበሩ፡፡ በዚህ ነፃና እንደልብ በሆነ ሕይወት ውስጥ ለሥራ፣ ለጥናትና ለሱባኤ ምቹ በሆነ አካባቢ ስለ እግዚአብሔር ተማሩ፡፡ ልጆቻቸውንም ስለ እርሱ ሥራና ስለ መንገዶቹ አስተማሩአቸው፡፡EDA 32.4

    እግዚአብሔር ለእስራኤል መሠረት እንዲሆን የፈለገው የማስተማሪያ ዘዴ ይህ ነው፡፡ ነገር ግን ከግብጽ እንዲወጡ ሲደረግ ከእስራኤላዊያን መካከል ልጆቻቸውን በማስተማር ረገድ ከእርሱ ጋር ለመሥራት ዝግጁ የነበሩ ጥቂቶች ብቻ ነበሩ፡፡ ወላጆቹ ራሳቸው መመሪያና ሥነ-ሥርዓት የሚያስፈልጋቸው ነበሩ፡፡ በእድሜልክ የባርነት ሰለባ ውስጥ ሆነው መኃይማን ያልሰለጠኑና የተናቁ ነበረ፡፡ ስለ እግዚአብሔር የሚያውቁት በጣም ትንሽ ስለነበረ በእርሱ ላይ የነበራቸው እምነታቸውም በጣም ትንሽ ነበረ፡፡ በውሸት ትምህርት የተምታታባቸው ነበሩ፡፡ ከአረመኔዎች ጋር በነበራቸው የቆየ ግንኙነርም ረክሰው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ሥነልቦናቸውን አንቅቶ ከፍ ለማድረግ አሰበ፡፡ ይኸን ዓላማውን ለማሳካትም ስለራሱ በማስተማር እውቀት ሊሰጣቸው ፈለገ፡፡EDA 33.1

    እርሱ ይዟቸው በበረሃ ሲጓሱ ሳለ በእያንዳንዷዋ ግራ ቀኝ እርምጃቸው ለረሀብ ውኃ ጥምና ድካም በተጋለጡ ጊዜ፤ በጠላቶቻቸው እጅ መከራ ላይ በወደቁ ጊዜ፣ ከዚያ ሁሉ ጭንቅ ረፍት ያገኙ ዘንድ ሲገላግሏቸው እግዚአብሔር ይገልጽላቸው የነበረው ያለማቋረጥ ለእነሱ ደህንነት ይሠራ የነበረውን ኃይል ቁልጭ አድርጐ በማስቀመጥ እምነታቸው እንዲጠናከር ይፈልግ ነበር፡፡ በእርሱ ፍቅርና ኃይል እምነት እንዲኖራቸው ካስተማራቸው በኋላ፣ በርሱ ሕግ መሠረተ ሃሣ ቦች ውስጥ በፀጋው ዘልቀው ይደርሱበት ዘንድ የሚገባቸውን የባሕሪይ ደረጃ እንዲያስተውሉ እፊታቸው ሊያቀርብላቸው ዓላማው ነበር፡፡EDA 33.2

    በሲናይ በረሃ በሚጓዙበት ጊዜ እስራኤላዊያን ይማሯቸው የነበሩ ትምህርቶች ክቡር ድንቅ ነበሩ፡፡ ከነዓንን ለመውረስ የማያስችላቸው ይህ የሥልጠና ጊዜ ነበር፡፡ ይህ አካባቢም የእግዚአብሔርን ዓላማ ለማስፈፀም የተመቻቸ ነበር፡፡ በሲና ተራራዎች ጥላ ሥር እስራኤላዊያን ድንኳኖቻቸውን ተክለው በሰፈሩበት ሜዳ የጉዞአቸው መሪ የሆነው የዳመና ምሰሶ ከመካከል ላይ ቆሞ ነበር፡፡ ማታ ማታ የእሳት አምድ በመሆን የመለኮትን ጥበቃ ያረጋግጥላቸው ነበር፡፡ በረፍት የመኝታ ሰዓትም የሰማይ መና በሰፈሩ በሙሉ በቀስታ ይወርድ ነበር፡፡ በጉዞ ሰዓት አንድ ክንድ በተራመድ ቁጥር እጅግ በጣም ሰፊ፤ አስከፊ ጋራ ሸንተረር ወጣ ገባ መሬት ቢሆንም ግርማ ሞገሳቸውንና ዘለዓለማዊነታቸውን ይናገሩ ነበር፡፡ ሰው ድንቁርናውንና ደካማነቱን ይረዳው ዘንድ «ተራሮችንና ኮረብቶችን በሚዛን የሚለካ ማን ነው?» ኢሳ 40፡12 ስለዚህ በራሱ ክብር መግለጫ ቅዱስ በሆነው ባህሪይውና በራሱ መስፈርቶች፤ ከኃጢአትና ከመተላለፍ ባሕሪይው እግዚአብሔር እስራኤልን ሊስብ ፈለገ፡፡EDA 34.1

    ይሁንና ሕዝቡ ትምህርቱን ለመቀበል ዳተኛ ነበር፡፡ በግብጽ እንደለመዱት በአካል የሚታዩ ጣኦት በሚያመልክ ወራዳ ፀባያቸው የማይታየውን አምላክ ባሕሪና ሕልውና ለመቀበልና ለማስተዋል ተሳናቸው፡፡ በዚህ ድክመታቸው እያዘነ እግዚአብሔር እርሱ በውስጡ እንዳለ የሚያሳይ ምልክት ሰጣቸው፡፡ «በመካከላቸውም አድር ዘንድ መቅደስ ሥሩልኝ፡፡ እኔ እንደማሳይህ ሁሉ፡፡» ዘፀ 25፡8 EDA 34.2

    ለእግዚአብሔር ማደሪያ የሚሆን መቅደስ በሚሠሩበት ጊዜ ሙሴ ማንኛውም በመቅደሱ ውስጥ የሚቀመጡ ዕቃዎች ሁሉ በሰማይ ባለው የአምላክ ማደሪያ ውስጥ እንዳሉት ንዋየ ቅዱሳት አስመስሎ እንዲሠራ ታዝዞ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ወደተራራ ጠራው፡፡ በሰማይ ያሉ ነገሮችን ሁሉ ገለጠለት፡፡ በእነዚያ ምሳሌም መቅደሱንና በውስጡም ለመቅደሱ አገልግሎት የሚገቡ ነገሮች ሁሉ በዚያ መልክ እንዲቀረፁ ነገረው፡፡EDA 34.3

    በመሆኑም መኖሪያ ቦታው እንዲሆንለት ላሰበው ለእስራኤል ሕዝብም ክብር የተሞላበትን የባሕሪውን ድንቅ ሀሳብ ገለፀላቸው፡፡ እግዚአብሔር በሙሴ ፊት በሲና ተራራ ላይ ባለፈ ጊዜ ሁኔታውን በምሳሌነት (እግዚአብሔር በመካከል ሲገኝ ምን እንደሚመስል) ገልጾላቸው ነበር፡፡ «እግዚአብሔርም በፊቱ አልፎ እግዚአብሔር፤ እግዚአብሔር፤ መሐሪ ሞገስ ያለው፤ ታጋሽም ባለብዙ ቸርነትና እውነት፡፡» ዘፀ 34፡6EDA 35.1

    ነገር ግን እነዚህን ክቡር ሀሳቦች በራሳቸው ሊደርሱባቸው የሚችሉት አልነበረም፡፡ በሲናይ ላይ የተደረገላቸው መገለጥ ደካሞችና እርዳታ የሚያስፈልጋቸው መሆኑን እንዲረዱ ብቻ ነው፡፡ ሌላው ትምህርት፤ የመቅደሱ ሥራ፤ የመስዋዕትነት አገልግሎት በማቅረብ፤ ስለሀጢአት ይቅርታ እና በአዳኑ አማካኝነት የሚገኘው ኃይል በሕይወት ውስጥ ታዛዥ ለመሆን እንደሚረዳ የሚያስተምራቸው ነበር፡፡EDA 35.2

    መቅደሱ ምሳሌ የሆነበት ዓላማ፤ የሚያምረው ሕንፃ፤ የግድግዳዎቹ የወርቅ ነፀብራቅ የሚያሳዩት የቀስተዳመና ጥላ፤ በኪሩቤል የእጅ ሥራ ጌጥ የተለጠፉ መጋረጃዎች፤ ዘለዓለም የሚቃጠለው ግሩም የዕጣን ሽታ ቤቱን ሲያወርደው፤ ቀሳውስት አንድ ነቁጥ የሌለበት ብሩህ ነጭ በሆነ የክህነት ልብስ፤ ጥልቅ ምስጢር ባለው የውስጥ ክፍል፤ በላዩም የምህረት ወንበር፤ የሚሰግዱ መላዕክትም ከወንበሩ ግራና ቀኝ የቅድስተ ቅዱሳን ክብር የተደረገበትን ሁሉ በክርስቶስ አማካኝነት እንዲፈፀም ነበር፡፡ እግዚአብሔር የእርሱ ሕዝብ በእነዚህ ነገሮች ሁሉ ዓለማውን እንዲረዱ ፈለገ፡፡ ከብዙ ዘመናት በኋላ ሐዋሪያው ጳውሎስ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ የተናገረው ያንኑ ዓላማ ነበር፡፡EDA 35.3

    «የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ እንደሆናችሁ የእግዚአብሔርም መንፈስ እንዲኖርባችሁ አታውቁምን? ማንም ..... የእግዚአብሔርን ቤተመቅደስ ቢያፈርስ እግዚአብሔር እርሱን ያፈርሰዋል፡፡ የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ ቅዱስ ነውና ያውም እናንተ ናችሁ፡፡» 1ኛ ቆሮ 3፡16-17EDA 36.1

    እስራኤላዊያን ቤተመቅደሱን እንዲያዘጋጁ ሲደረግ የተሰጣቸው እድልና ክብር እጅግ ታላቅ ነበር፡፡ በተጣለባቸው ኃላፊነትም የላቀ ነበር፡፡ ከመጠን በላይ ግሩም ድንቅ የሆነ ሕንፃ፤ እጅግ በጣም ውድ የሆኑ የግንባታ ዕቃዎችን የጠየቀ፤ የተራቀቀ የእጅ ጥበብ የሚያስፈልገው ሕንፃ በበረሃ መካከል ገና ከባትነት በወጡ ሕዝቦች እጅ መሠራት ነበረበት፡፡ በእውነቱ እጅግ የሚያስገርምና የሚያስደንቅ ግዳጅ ነበር የተሰጣቸው፡፡ ነገር ግን የህንንውን ፕላን የሰጣቸው ጌታ ከግንበኞቹ ጋር አጠገባቸው ሆኖ ይረዳቸው ነበር፡፡EDA 36.2

    «እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ብሎ ተናገረ እይ! ከይሁዳ ነገድ የሚሆን የሆር የልጅ ልጅ የኡሪ ልጅ ባስልኤልን በስሙ ጠርቼዋለሁ በሥራ ሁሉ ብልሃት በጥበብም በማስተዋልም በእውቀትም የእግዚአብሔርን መንፈስ ሞላሁበት የጥበብንም ሥራ ያስተውል ዘንድ በወርቅና ብር በናስም ይሠራ ዘንድ ለፈርጥ የሆነውን የእንቁ ድንጋይ ይቀረጽ ዘንድ እንጨቱንም ይጠርብ ዘንድ ሥራውንም ሁሉ ይሠራ ዘንድ፡፡ እኔም እነሆ ከርሱ ጋር ከዳን ነገድ የሚሆን የአሂላሜክን ኤልያብን ሰጠሁ፡፡ ያዘዝሁህን ሁሉ ያደርጉ ዘንድ በልባቸው ጥበበኞች በሆኑት ሁሉ ጥበብን አኖርሁ፡፡» ዘፀ 31፡1-6EDA 36.3

    ክርስቶስና የርሱ መላዕክት መመሪያ ይሰጡበት የነበረው በምድረ በዳው የተቋቋመው ያ ት/ቤት ምንኛ በሚደነቅ የእጅ ጥበባት የተሠራ ነበር? ቤተ መቅደሱን በማዘጋጀትና ውስጡን በማሟላት ረገድ ሕዝቡ በሙሉ መተባበር ነበረበት፡፡ ለአዕምሮና ለእጅ የሚሆን ሥራ ሞልቶ ነበር፡፡ እጅግ በጣም ብዙ ልዩ ልዩ ነገሮች አስፈላጊ ነበሩ፡፡ ሁሉም ሰው ልቡና አቅሙ የፈቀደውን ያክል እንዲያበረክት ተጋብዞ ነበር፡፡EDA 37.1

    በመሆኑም በመሥራትና በመስጠትም ከእግዚአብሔር ጋርና እርስ በራሳቸውም መተባበርን ይማሩ ነበር፡፡ የእግዚአብሔርን መቅደስ በልባቸው ውስጥ የመገንባት መንፈሳዊ ሥራ በሕብረት መሥራት ተማሩ፡፡EDA 37.2

    ከግብጽ ከወጡበት ጊዜ ጀምሮ በጉዞአቸው ሁሉ የሙያ ሥልጠናና የሥነ-ሥርዓት ትምህርት ይሰጣቸው ነበር፡፡ ግብጽን ከመልቀቃቸው በፊትም በጊዜያዊነት የተቋቋመ ዝግጅትና አደረጃጀት ነበራቸው፡፡ በሲና ደግሞ የአደረጃጀቱ ጠቅላላ ዝግጅት ተሟልቶና ተጠናቅቆ ነበር፡፡ በእግዚአብሔር ሥራዎች ውስጥ የነበረው የሚያስደንቅ የተሟላ ሥርዓት በእብራዊያን ኢኮኖሚ በሚገባ ተገልጾ ነበር፡፡ እግዚአብሔር የስልጣንና የመንግሥት ማዕከል ነበር፡፡ ሙሴ ደግሞ የርሱ ወኪል የነበረ እንደመሆኑ ሕጐቹን በርሱ ስም የሚያስፈጽም ነበር፡፡ ከዚያ በታች የሰባዎቹ ምክር ቤት አባላት፤ በዚያ ሥር የካህናት፤ ከዚያም መሳፍንት ነበሩ፡፡ በእነርሱም ሥር «የሻለቆችም፤ የመቶ አለቆችም፤ የሃምሳ አለቆችም፤ የአሥር አለቆችም» (ዘሁ 11፡16-17 ዘዳግ 1፡15) በመጨረሻም ለልዩ ልዩ ተግባራት የተመረጡ መኮንኖች ነበሩ፡፡ ጠቅላላ ስፍራው በፍፁም ሥነሥርዓት ተሟልቶ ተደራጅቶ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ማረፊያ የሆነው ቤተመቅደስ በመካከል ላይ ነበር፡፡ የአገልጋይ ካህናትና ሌቪያዊያን ድንኳኖች በዙሪያው ነበሩ፡፡ ከዚህ ውጪ እያንዳንዱ ነገድ በየደረጃው ሰፈረ፡፡EDA 37.3

    በዚህ ሂደት የንጽህና ትምህርትና ደንቦችም ተግባራዊ ይሆኑ ነበር፡፡ በሕዝቡ ላይም እንደ ትዕዛዝ ተጥሎ ነበር፡፡ ምክንያቱም ለጤና አስፈላጊ መሆናቸው ብቻ ሳይሆን ቅዱስ የሆነውን አምላክ በመካከላቸው በማግኘታቸውም ነው፡፡ በመለኮት ሥልጣን ሙሴ ለነሱ ተናገራቸው፡፡ «አምላክህ እግዚአብሔር ሊያድንህ .... በሰፈርህ መካከል ይሄዳልና ........ ስለዚህ ሰፈርህ የተቀደሰ ይሁን፡፡» ዘዳ 23፡14EDA 38.1

    የእስራኤሎች ትምህርት የኑሮ ወግና ባህላቸውንም ያካተተ ነበር፡፡ ደህንነታቸውን የሚመለከት ማናቸውም ነገር ሁሉ የመለኮት ፍላጐት ነበር፡፡ እናም ከመለኮት ሕግ ተከፍሎ የመጣ ሕግም ነው፡፡ ምግባቸውን በማቅረብ በኩል እንኳ እግዚአብሔር ከፍተኛውን በጐ ነገር ያስብላቸው ነበር፡፡ በምድረ በዳ የሰጣቸው መና አካልን፣ አእምሮንና መንፈሳዊ ብርታትን የሚሰጥ ነበር፡፡ ምግቡ የተወሰነ ወይም አንድ ዓይነት ብቻ በመሆኑ ብዙዎቹ ቢያምጹም፣ ወደኋላ ተመልሰው በድሮው ትዝታ «;በስጋ ምንቸት አጠገብ ተቀምጠን እንጀራ ስንበላ ስንጠግብ ሳለን» አሉ ዘፀ 16፡3 ነገር ግን ለእነርሱ አነጋገር እግዚአብሔር በጥበብ የመረጠላቸው መልስ ተቃራኒውን ስለነበር መካድና ምንም መናገር አልቻሉም፡፡ በምድረበዳው ሕይወታቸውን አስቸጋሪነት በመገንዘብ ከማንኛውም ነገድ መካከል ደክሞት በበረሃ የቀረ አልነበረም፡፡EDA 38.2

    በጉዞአቸው ሁሉ የእግዚአብሔርን ሕግ የያዘው ቅስት መንገዱን ይመራቸው ነበር፡፡ የሚያርፉበትን ሰፈርም ሁልጊዜ የዳመናው አምድ እየወረደ ያሳያቸው ነበር፡፡ ዳመናው በመቅደሱ ላይ አርፎ በቆየበት ጊዜ ሁሉ እነሱም እንደሰፈሩ ይቆያሉ፡፡ ሲነሳ ሳለ ጉዞአቸውን ይቀጥላሉ፡፡ ለረፍትም ሆነ የጉዞ ንቅናቄ ከመጀመሩ በፊት የጽሞና ፀሎት ይደረጋል፡፡ «ሙሴም ታቦቱ በተጓዘ ጊዜ አቤቱ ተነሳ ጠላቶችህም ይበተኑ የሚጠሉህም ይበተኑ የሚጠሉህም ከፊትህ ይሽሹ ይል ነበር፡፡ EDA 38.3

    ባረፈ ጊዜም አቤቱ ወደእስራኤል እልፍ አእላፋት ተመለስ ይል ነበር፡፡» ዘሁልቁ 10፡35-36EDA 39.1

    ሕዝቡ በምድረ በዳው በሚጓዝበት ጊዜ በጣም ብዙ ግሩም ድንቅ ትምህርቶች በመዝሙሮች አማካኝነት በአእምሮአቸው ውስጥ ይቀረጽ ነበር፡፡ ከፈርኦን ጦር አምልጠው ከተረፉበት ጊዜ ጀምሮ ጠቅላላ ሠራዊተ እስራኤል የድል መዝሙር በአንድነት ይዘምሩ ነበር፡፡ ከበረሃውና ከባሕሩ አልፎ የደስታ መዝሙር አዝማች ሲደጋገም ተራራዎቹም ስለሚያስተጋቡ ዘወትር የምሥጋና ዜማ ይሰማ ነበር፡፡ «በክብር ከፍ ከፍ ብሏልና ለእግዚአብሔር ዘምሩ» ዘፀ 15፡21 በጉዞ ላይ ይህ መዝሙር ዘወትር ይዘመር ነበር፡፡ የበርሃ ተጓዥ መናኞችን ልብ እያስደሰተ የእምነት ቀንዲልም ያበራላቸው ነበር፡፡ በሲና የተሰጧቸው ትዕዛዞች የእግዚአብሔር ፍቅርና እነሱን ለማዳን የተደረገ አስገራሚ ሥራዎቹ ታሪኮች ተስፋ በመለኮት አመራር በመዝሙር ውስጥ ተገልፀው ነበር፡፡ ከሙዚቃ መሣሪያዎች ጋርም ተቀነባብረው ድምጻቸው በምስጋና ዜማ ተዋህዶ አዝማቾቹን ጠብቀው ያስተጋቡ ነበር፡፡EDA 39.2

    በመሆኑም በወጣ ገባው አስቸጋሪ መንገድ የሚጓዙበት ጊዜ ሐሳባቸው ይነቃቃላቸው ነበር፡፡ ረፍት የሌለውና ከቁጥጥር ውጪ የነበረው መንፈሳቸው ተገርቶና ተረጋግቶ ይቀዘቅዝ ነበር፡፡ በአእምሮአቸው ውስጥም የእውነት መሠረተ ሀሳቦች ተተክተው ነበር፡፡ እምነታቸውም ተጠናክሮ ነበር፡፡ የተግባር የመዝሙር ዝግጅት ሥርዓትን አንድነትን አስተማራቸው፡፡ ሕዝቡም ከእግዚአብሔር ጋር እና እርስ በራሳቸውም እንዲቀራረቡ አደረጋቸው፡፡EDA 39.3

    እግዚአብሔር ለእስራኤል በሚያደርገው ሁሉ በአርባ ዘመናት የበረሃ ጉዞ ውስጥ ሙሴ እንዲህ ብሎ ተናገረ «ሰውም ልጁን እንደሚገስጽ፤ እንዲሁም አምላክ እግዚአብሔር አንተን እንዲገስጽ በልብህ አስተውል፡፡» «በልብህ ያለውን ትዕዛዝ ትጠብቅ ወይም አትጠብቅ እንደሆን ያውቅ ዘንድ፡፡» ዘዳ8፡52EDA 39.4

    «የነፋስ ጩኸትም በሞላበት ውድማ አገኘው፤ ከበበውም፤ ጠነቀቀለትም፡፡ እንደ ዐይን ብሌን ጠበቀው፡፡ ንስር ጫጩቶቹን እንደሚያወጣ በርሱም ላይ እንደሚሰፍ ክንፎቹን ዘርግቶ ወሰዳቸው፡፡ በክንፎቹም አዘላቸው፡፡ እግዚአብሔር ብቻውን መራው፡፡ ከርሱም ጋር ሌላ አምላክ አልነበረም፡፡» ዘዳ 32፡10-12 EDA 40.1

    «ለአብርሃም ለባርያው የነገረውን ቅዱስ ቃሉን አስቦአልና፡፡ ሕዝቡንም በደስታ የተመረጡትንም በእልልታ አወጣ፡፡ የአህዛብንም አገሮች ሰጣቸው፡፡ የወገኖችንም ድካም ወረሱ ሕጉን ይጠብቅ ዘንድ፡፡» መዝ 105፡42-45፡፡EDA 40.2

    እግዚአብሔር ለእስራኤል የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ አሟልቶ ሰጣቸው፡፡ ለእርሱ ስም ክብርና በአካባቢያቸው ለሚኖሩ ሕዝቦችም በረከት ሊሆኑ የሚያስችላቸውን ነገር ሁሉ ሰጣቸው፡፡ ትዕዛዙን በማክበር መንገድ ከሄዱ «አህዛብ ሁሉ በምስጋና፤ በስም፣ በክብር ከፍ ያደርጓቸው ዘንድ» ቃል ገባላቸው፡፡ የምድር አህዛብም ሁሉ የእግዚአብሔር ስም በአንተ ላይ እንደተጠራ አይተው ይፈሩሃል፡፡» አህዛብም የተደረገውን ሁሉ አይተው እንዲህ ይላሉ «በእውነት ይህ ታላቅ ሕዝብ ጠቢብና አስተዋይ ህዝብ ነው፡፡» ዘዳግ 26፡19 ምዕ 28፡10 ምዕ 4፡6EDA 40.3

    ለእስራኤል በተሰጠው ትዕዛዝ ላይ ትምህርትን በሚመለከት ግልጽ መመሪያ ተቀምጧል፡፡ በሲና በረሃ ላይ እግዚአብሔር ለሙሴ ራሱን የገለጠለት «;መሐሪ ሞገስ ያለው፣ ታጋሽ፣ ባለብዙ ቸርነትና እውነት» በመሆኑ ነው፡፡ በእርሱ ሕግ ውስጥ የተካተቱ እነኝህ መሠረታዊ ሐሳቦች እስራኤላዊያን ወላጆች ልጆቻቸውን ያስተምሩበት ዘንድ ነው፡፡ ሙሴም በእግዚአብሔር አመራር እንዲህ ሲል ገለፀላቸው፡፡ «እኔም ዛሬ አንተን የማዝዘውን ይህን ቃል በልብህ ያዝ ለልጆችህም አስተምረው፡፡ በቤትህም ስትቀመጥ በመንገድም ስትሄድ ስትተኛም ስትነሳም ተጫወተው፡፡» ዘዳግ 6፡67EDA 40.4

    እነኝህ ነገሮች በደረቅ ንድፈ ሐሳብነታቸው ብቻ መስተዋል የለባቸውም፡፡ እውነትን ማካፈል ያለባቸው ሰዎች መጀመሪያ መሠረታዊ ሐሳቦቹን ራሳቸው ገቢራዊ ማድረግ አለባቸው፡፡ በራሳቸው ሕይወት ውስጥ የእግዚአብሔርን ባሕሪይ በቅድስና በትክክለኛ ቀናነት እና ራስን ባለመውደድ ሲያንፀባርቁ ብቻ ነው ሌሎችን መሳብ የሚችሉት፡፡EDA 41.1

    እውነተኛ ትምህርት ባልተዘጋጀና በማይቀበል አእምሮ ውስጥ መመሪያዎችን በግዴታ መስጠት አይደለም፡፡ የአእምሮ ኃይል መነቃቃትና ፍላጐቱም መነሳሳት ያሸዋል፡፡ ለዚህም ከእግዚአብሔር የተሰጠ የመማሪያ ዘዴ አለ፡፡ አእምሮን የፈጠረና አሰራሩንም የቀለጠፈ እንዲሆን ያደረገ እድገቱም በዚያው መልክ እንዲሆን አድርጐ አዘጋጅቶታል፡፡ በቤታቸውና በቤተመቅደስ ውስጥ በተፈጥሮና ሥነጥበብ አማካይነት በሥራና በመዝናኛ ሰዓት፤ በእግዚአብሔር ቤትና ለመታሰቢያ በሆነው አለት፤ በዘዴና በተቀደሰ ሥርዓት ቁጥር በሌላቸው ምልክቶችም እግዚአብሔር የእርሱን መርሆዎች በመግለጽ እና ድንቅ ሥራዎቹንም በመታሰቢያነት በማቆየት ለእስራኤላዊያን ትምህርት ሰጥቷል፡፡ ከዚያ በኋላ ጥያቄ ሲነሳ የተሰጠው መመሪያ አዕምሮንና ልብን የሚስብ ሆኖ ተገኝቷል፡፡EDA 41.2

    ለተመረጡት ሕዝቦች የሚሆን ትምህርት በሚዘጋጅበት ጊዜ በእግዚአብሔር ላይ ያተኮረች ሕይወት ፍፁም የተሟላች ሕይወት እንደምትሆን ግልጽ ተደርጓል፡፡ በውስጧ እርሱ ባበቀለው ፍላጐት ሁሉ የሚረካበትንም አዘጋጅቶለታል፡፡ ከፍሎ የሰጠውን ክህሎት ሁሉ የሚያድግበትን መንገድ ከፍቷል፡፡EDA 41.3

    የውበት ሁሉ ተራኪ፤ ራሱም ውበትን አድናቂ የሆነ አምላክ የውበትን ፍቅር በልጆቹ ውስጥ ሰርጾ እንዲያረካቸው አደረገ፡፡ ለማህበራዊ ፍላጐቶቻቸውም፤ ለመተዛዘን ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርገውንና ሕይወትን የሚያጣፍጥና የሚያበራውን የዋህነትንና ተባባሪነትንም ሰጣቸው፡፡ እንደ አንድ የትምህርት መሣሪያ በእስራኤላዊያን የደስታ በዓላት ውስጥ አንድ ዋነኛ ቦታ ነበረ፡፡ በአዘቦት ቀን ቤታቸው እንደ ት/ቤት እና እንደ ቤተክርስቲያንም ነበር፡፡ በተለየና ኃይማኖት ነክ በሆነ ጉዳይ ላይ ወላጆች እንደአስተማሪ የሚሆኑበት ነበር፡፡ ነገር ግን በዓመት ሦስት ጊዜ ለማህበራዊ ግንኙነትና አምልኮ የተመረጡ ጊዜዎች ነበሩ፡፡ እነኝህ ስብሰባዎች በመጀመሪያ በሸሎ በኋላም በየሩሳሌም ይካሄዱ ነበር፡፡ ቀደም ሲሉ አባቶችና ወንዶች ልጆች ብቻ ነበሩ፡፡ እንዲሰበሰቡ የሚፈቀድላቸው፡፡ ነገር ግን ይኸንን ዕድል ማንኛውም ሰው እንዲያመልጠው አይፈልግም ነበር፡፡ እናም በተቻለ መጠን ሁሉም በቤት ውስጥ ያለ የቤተሰብ አባል የሆነ ሰው ከነሱ ጋር በእንግድነት ያለ ሁሉ አብዛኛውን ጊዜም ሌዋውያንና ሌሎች ድሆች ይገኙ ነበር፡፡EDA 42.1

    ወደ እየሩሳሌም ይደረግ የነበረው ጉዞ ቀላልና ክብር ያለው ሰው ወይም የታቦት ጉዞ ዓይነት ነበር፡፡ ውበት በተጐናፀፈው የበልግ ወራት፤ በሞላው ክረምት አጋማሽ ላይ፤ ወይም በፀደይ የእሸት ወራት የሚደረግ ጉዞ እጅግ የሚያስደስት ነበር፡፡ ልጅ አዋቂ ሽማግሌ ሳይባል ከእግዚአብሔር ጋር በተቀደሰው መኖሪያው ለመገናኘት ሁሉም ስጦታዎቻቸውን ይዘው ይመጡ ነበር፡፡ በጉዞ ላይ ያለፉ ገጠመኞቻቸውን፤ የድሮ ታሪካቸውን፤ ሽማግሌዎችም ወጣቶችም በጣም ይወዷቸው የነበሩ ታሪኮች ለእብራዊያን ልጆች ይነገራቸው ነበር፡፡ የምድረ በዳውን ጉዞ ያሞቁት የነበሩ መዝሙሮችን አስታውሰው አሁንም ይዘምሯቸው ነበር፡፡ የእግዚአብሔርን ትዕዛዞች ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ይደግሟቸው ነበር፡፡ እናም በተባረኩ የተፈጥሮ መስህቦች ውበት ተማርከውና ፤ ደግነት የተሞላበት የሰው ልጆች ማህበራዊ ግንኙነት፣ እጅግ ብዙ ሕፃናትና ወጣቶች እነዚህ ትዝታዎች ሲጓዙ ለዘለዓለም በአእምሮአቸው ውስጥ ተቀርፀውባቸው ቀርተዋል፡፡EDA 42.2

    እነኝህ በእየሩሳሌም ይከበሩ የነበሩ የክብረ በዓል ዝግጅቶች ከፋሲካ በዓል አገልግሎት ጋር ተያይዞ የማታ ስብሰባዎች፤ አዋቂዎች በወገባቸው ላይ ድጋቸውን እንዳሰሩ ጫማቸውን እንዳጠለቁ፤ ምርኩዞቻቸውን በእጃቸው ይዘው፤ ምግብ ጠቦት፣ ያልቦካ ዳቦ፤ መራራ ቅጠል፤ በጽሞና ፀሎት ላይ የሚረጨው ደም ታሪክና ዝማሬ፤ የሞት መለአክ፣ ከእስር መፈታታችን የሚያመለክተው የሰልፍ እርምጃ እነኝህ ሁሉ ሀሳብን የሚቀሰቅሱና ልብን የሚማርኩ ነበሩ፡፡EDA 43.1

    የቤተ መቅደሱ ድግስ ወይም የመከር ስብሰባ ድግሥ፤ ካታክልት ቦታ ወይም የዱር ፍራፍሬ፤ በፀሎት ሳምንት ያለው ማህበራዊ ግንኙነት የቅድስና ማስታወሻ አገልግሎት ፣ በመቅደስ ውስጥ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ሌዋውያን ይለገሱ የነበሩ በርካታ ስጦታዎች ልጆቹ ለሆኑት ለእንግዶችና ለድሆች በመስጠት ይደረግ የነበረው ክንውን ሁሉ፤ ዓመቶን በሙሉ በቸርነት ወደ ታደገ፤ መንገዱንም ሁሉ ለስላሳ ወዳደረገ አእምሮን በምስጋና የሚያነሳሳ ነበር፡፡EDA 43.2

    በእስራኤል ፀሎት ውስጥ ከአመት ውስጥ አንድ ሙሉ ወር የሚያክል ጊዜ በዚህ ዓይነት ተግባር ያልፋል፡፡ ከጥበቃና ከሥራ ሁሉ ነፃ የሆነ ጊዜ ነበር፡፡ ሙሉ በሙሉ ልባቸውን የሚያስገዙበት ጊዜ በእውነተኛው አነጋገር ዓላማው ትምህርትን ለማግኘት ነበር፡፡EDA 43.3

    ለውርስ ተገቢ የሆነውን የራሱን ሕዝብ በመምረጥ ረገድ እግዚአብሔር ምርጦቹንና ከእነሱም በኋላ ለሚመጡ ትውልዶች ሁሉ የመሬት ባለቤትነትን ትክክለኛውን ሐሳብ ማስተማር ዓላማው ነበር፡፡ የከነዓን ምድር ሌዋውያን ብቻ የመቅደስ አገልጋይ በመሆናቸው ሲቀሩ በስተቀር ለሁሉም ነገዶች እኩል ተከፋፈለች፡፡ አንድ ሰው በሆነ ምክንያት ለተወሰነ ወቅት ብቻ የመሬት ባለቤትነቱን ቢለቅ እንኳ የልጆቹን የመውረስ መብት ግን ሊሸጥ አይችልም፡፡ ባለቤትነቱን ለተወሰነ ጊዜ ቢለቅ በሚፈልገው በማንኛውም ጊዜ ሁሉ መልሶ መውሰድ ይችላል፡፡ የብድር ዕዳም ቢኖር በየሰባት ዓመት ይሰረዛል፡፡ በሃምሳ ዓመት በእዮቤልዩ ዘመን ላይ የመሬት ይዞታ ውል ሁሉ ይታደሳል፡፡ ለቀድሞው ባለቤትም ይመለስለታል፡፡ ስለዚህም እያንዳንዱ ቤተሰብ የመሬት ባለይዞታነቱ ይጠበቅለታል ማለት ነው፡፡ እንዲሁም ለሀብትና ለንብረትም ሆነ ለመሬት ወግ አጥባቂዎች የደህንነት ማረጋገጫ ተሰጥቷቸው ነበር፡፡EDA 43.4

    መሬቱን ለህዝቡ በማከፋፈል ረገድ እግዚአብሔር በኤደን ይኖሩ ለነበሩት እንዳደረገው ሁሉ ለልማት ተስማሚ የሆነውን መሬት ለአትክልትና ለእንስሳት እርባታ እንክብካቤ ያደርጉት ዘንድ ሰጣቸው፡፡EDA 44.1

    ሌላው ለትምህርት እንዲሆን እግዚአብሔር በተጨማሪ የሰጣቸው ነገር በየሰባቱ ዓመት አንድ ጊዜ የሚደረገው ማሳውን እንዲሁ ማሳደርና ከዚያም አልፎ አልፎ የሚበቅለውን ገቦ የሚያስገኘውን ምርት ለድሆች መተው ነው፡፡ በዚህም ዘወትር ኑሮን ለማሸነፍ በሥራ ከመጠመድ እንዲህ ዓይነት ለማህበራዊ ግብቡነትና ለአምልኮት፤ ደግነትና ቸርነትን ለመለማመድ፤ ሰፋ ያለ የጥናት ዕድል ተሰቷቸው ነበር፡፡EDA 44.2

    የመሬት ክፍፍልን በተመለከተ የእግዚአብሔር ሕግ መሠረታዊ ሐሳቦች በዛሬዋ ዓለማችን በሚገባ ሥራ ላይ ቢውሉ ኖሮ የሕዝቡ ሕይወት ምን ያክል የተለየ በሆነ ነበር እነኝህ መሠረታዊ ሀሳቦች በሚገባ ቢስተዋሉ ድሀውን በሀብታም ከመጨቆን፤ ሀብታሙንም በድሀው ከመጠላት የተነሳ በዓለም ላይ በዘመናት ሁሉ ከደረሱት ጭንቅና መከራዎች በተከላከሉልን ነበር፡፡ ይህም ብዙ ሀብት ማጋበስን የሚከላከል ሲሆን በሽህና በአሥር ሽህ የሚቆጠሩ አሽከርና ገረዶች በመሆን የተጐዱ ሰዎችን ከድንቁርና ውርደት ወደነዚህ እጅግ ድንቅ የሆኑ መልካም ዕድሎች እንዲዞሩ ለማድረግ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡ አሁን ዓለምን ለማጥለቅለቅ ከሚያሰጋት የሥርአት አልበኝነትና ደም መፋሰስ ችግሮችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ይረዳል፡፡EDA 44.3

    ከምናገኘው ከማናቸውዋ በረከት ለእግዚአብሔር አሥራት መክፈል፤ ከአትክልት ፍሬም ሆነ፤ ከእርሻ ምርት፤ ከበጐችና ከከብቶች መንጋ፤ ወይም ከአእምሮም ሆነ ከእጅ ሥራ ውጤት እንደአሥራት ሁሉ ሁለተኛውን ከልብ የሚደረግ ልግሥናና ለድሀ መቸር እና ሌሎች ተመሳሳይ ጠቀሜታ ያላቸው በጐ አድራጐቶች እግዚአብሔር የሁሉ ነገር ባለቤት የመሆኑን እውነታና የእርሱ በረከት መውረጃ የመሆን እድላቸውን በአዲስ መልክ ለሕዝቡ ይገልጽላቸዋል፡፡ እየጠበበ የሚሄድ የራስ ወዳድነትን መንፈስ ለመግደልና ወዲያ ለመጣል በምትኩም በሕሪይን ለማስፋፋትና ክቡር ለማድረግ የሚሰጥ ሥልጠና ነው፡፡EDA 45.1

    ስለ እግዚአብሔር የሚኖር እውቀት በጥናትና በሥራ ወደ እርሱ ዘንድ የመቅረብ በባሕሪይና የርሱን ተምሳሌት መያዝ ለእስራኤላዊያን የተሰጠውን ትምህርት መሠረት መንገድና ዓላማ ነበር፡፡ ይህም ትምህርት ከእግዚአብሔር ለወላጆች በእነርሱ በኩልም ለልጆቻቸው የተሰጠ ነበር፡፡EDA 45.2

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents