Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents
ሥነ - ትምህርት - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ምዕራፍ 1—የእውነተኛው ትምህርት ምንጭና ዓላማ

    «የቅዱሳን ዕውቀት ማስተዋል ነው፡፡»
    «ራስህን ከእርሱ ጋር አስተዋውቅ፡፡»
    EDA 8.1

    ስለ ትምህርት ያለን አስተሳሰብ በጣም ጠባብና ዝቅተኛ ነው፡፡ ስፋት ያለው አስተሳሰብና ከፍተኛ ዓላማ ሊኖረን ያሻል፡፡ እውነተኛ ትምህርት በአንድ የጥናት መስክ ምርምር ከማድረግም በላይ ነው፡፡ ዕለታዊ ኑሮአችንን ለማሸነፍ ከመዘጋጀትም የበለጠ ነው፡፡ ሁለንተናዊ ሕይወታችንና እስከ እድሜአችን መጨረሻ ያለውን ጊዜአችንን የሚመለከት ነው፡፡ የአካላዊ ፣ የአእምሮና፣ የመንፈሳዊ ኃይል የተቀናጀ ዕድገት ማለት ነው፡፡ ተማሪው በዚህ ዓለም ሲያገለግል ደስተኛ እንዲሆንና በመጪውም ዓለም በስፋት እያገለገለ የላቀ ደስታ እንዲያገኝ የሚያዘጋጀው ነው፡፡EDA 8.2

    የዚህ ዓይነቱ ትምህርት ምንጭ እግዚአብሔር መሆኑ ሊገለጥልን የሚችለው ቅዱስ መጽሐፍት ወሰን ወደሌለበት አምላክ ሲያመለክቱ ነው፡፡ «የጥበብና የዕውቀት መዝገብ ሁሉ የሚገኘው በርሱ ዘንድ ነውና፡፡» (ቆላ 2፡3) «ከእርሱ ጋር ጥበብና ኃይል ማስተዋልም አለ፡፡» ኢዮብ 12፡13EDA 8.3

    ዓለማችን ሰፊ ምርምር ያካሄዱ ድንቅ ክህሎታቸው የሰዎችን አስተሳሰብ የሚቀሰቅስ፣ ለመጠቀ ዕውቀት በር የከፈቱ ትልልቅ ሊቃውንት ነበሯት፡፡ እነዚህ ሰዎች ደግሞ በወገኖቻቸው ዘንድ እንደ መሪና እንደ ትልቅ በጐ አድራጊ ተከብረው ኖረዋል፡፡ ነገር ግን ከእርሱ በላይ የላቀው ጌታ አለ፡፡ በዓለም ላይ የነበሩ ዕውቅ ምሁራንን ታሪክ ወደ ኋላ መለስ ብለን ታሪክ እስከመዘገበው ድረስ ያለውን ልንመረምር እንችላለን፡፡ የዓለም ብርሃን ግን ከእነሱ በፊት ገና እምቅድመዓለም ነበረ፡፡ በፀሐይ ዙሪያ የሚገኙ ጨረቃና ከዋክብት ከፀሐይ የሚያገኙትን ብርሃን በማንፀባረቅ እንደሚያበሩልን ሁሉ በዓለማችን የሚገኙ ሊቃውንት እውነትን እስካስተማሩ ድረስ የጽድቅ ፀሐይ ከሆነው ብርሃን ተቀብለው ያንፀባርቃሉ፡፡ እያንዳንዱ የሚፈልቀው ሐሳብ፣ እያንዳንዱ የዕውቀት ብልጭታ የዓለም ብርሃን ከሆነው አምላክ የሚመነጭ ነው፡፡EDA 8.4

    በአሁኑ ጊዜ ስለከፍተኛ ትምህርት አሰጣጥ አስፈላጊነት ብዙ ይነገራል፡፡ እውነተኛው ከፍተኛ ትምህርት የሚገኘው «የጥበብና የኃይል ባለቤት ከሆነው (ኢዮብ 12፡13) «ዕውቀትና ማስተዋል የሚገኙት ከእርሱ ዘንድ ነው፡፡ ከተባለለት አምላክ ነው፡፡» ምሳሌ 2፡6፡፡EDA 9.1

    የእውነተኛ ዕውቀትና ትክክለኛ ዕድገት ምንጭ እግዚአብሔርን ማወቅ ነው፡፡ በኃጢአት ከተበከለው ውጪ በአካላዊ በአእምሮና በመንፈሳዊ መስክ በምንመለተው አድማስ ሁሉ ይህ ዕውቀት ይገለጣል፡፡ በንፁህ ልቦና ተነስተን እውነት ላይ ለመድረስ ስንል የትኛውንም የምርምር መስመር ብንከተል ከማይታየው ኃይል ጋር መገናኘታችን አይቀርም፡፡ በዚህ ጊዜ የሰው ሀሳብ ከእግዚአብሔር ጋር ፣ ውስን የሆነው፣ ወሰን ከሌለበት ኃይል ጋር ይገናኛል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ግንኙነት በአካል በአእምሮና በመንፈስ ላይ የሚያሳድረው በጐ ለውጥ ለግምት የሚያዳግት ነው፡፡EDA 9.2

    እጅግ ታላቁ ከፍተኛ ትምህርት የሚገኘው በዚህ ግንኙነት አማካይነት ነው፡፡ ይህም የእግዚአብሔር የራሱ የዕድገት ማበልፀጊያ ዘዴ ነው፡፡ እርሱ ለሰው ዘር ሁሉ የሚያስተላልፈው መልዕክት «ራስህን ከርሱ ጋር አስተዋውቅ፡፡» የሚል ነው፡፡ (ኢዮ 22፡21) በእነኝህ ቃላት የተጠቀሱት የትምህርት ዘዴዎች የሰው ልጆች አባት ለሆነው ለአዳም በተሰጡት ትምህርቶች የተሠራባቸው ዘዴዎች ናቸው፡፡ አዳም ያለሀጢአት በኤድን ውስጥ በንጽህናና በክብር ሙሉ ሰውነት በነበረ ጊዜ ያስተምረው የነበረው ያ አምላክ ነው፡፡EDA 9.3

    በትምህርት ሂደት ውስጥ መጠቃለል ያለበትን ቁም ነገር ለመረዳት የሰውን ተፈጥሮአዊ ባሕርይና እግዚአብሔር ለምን ዓላማ እንደፈጠረው ማገናዘብ ያስፈልጋል፡፡ በተጨማሪም ሰው ክፉውን ካወቀ ወዲህ ሁኔታው እንዴት እንደተለወጠና እንደዚያም ሆኖ እያለ እግዚአብሔር የሰውን ዘር ለማስተማር ያወጣውን ክቡር ዕቅድ አገናዝቦ መመልከት ያስፈልጋል፡፡EDA 10.1

    አዳም በእግዚአብሔር እጆች ተሠርቶ እንደወጣ በአካላዊዩ፣ በአእምሮውና መንፈሳዊ ተፈጥሮው ውስጥ የፈጣሪውን ተምሳሌት ይዞ ወጣ፡፡ «እግዚአብሔር ሰውን በራሱ መልክና አምሳያ ፈጠረው፡፡» (ዘፍ. 1፡27) ከዚያም በኋላ የእግዚአብሔር ዓላማ ሰው በእድሜው እየጨመረ በሄደ መጠን ይኸንን የእግዚአብሔር ተምሳሌነቱን ይበልጥ እያጐላው እንዲሄድና የፈጣሪውን ክብርና ሞገስ እያደር የበለጠ እንዲያንፀባርቀው ነበር፡፡ የአእምሮ ችሎታውና ጥንካሬ ያለማቋረጥ እየዳበረ እንዲሄድ ነበር፡፡ ይኸንን ብቃቱንም ገቢራዊ ለማድረግ እጅግ ሰፊ ዕድል ተሰጥቶት ነበር፡፡ የሚመራመሩበት መስክም ክብር የተሞላበት ነበር፡፡ በገሃድ የሚታዩት ዓለማት ምስጢር «በፍፁማዊ እውቀት የተራቀቁት አስገራሚ ሥራዎቹ» (ኢዮ 37፡16) የሰው ልጆችን የማጥናት ፍላጐት ጋበዙ፡፡ ከፈጣሪው ጋር የነበረው ፊት ለፊትና ልብ ለልብ የሆነ ግንኙነት ለሰው ልጅ እጅግ ታላቅ ዕድል ነበር፡፡ ታማኝ በመሆን ፀንቶ ቀጥሎበት ቢሆን ኖሮ ይህ ሁሉ ለዘለዓለም የርሱ ሆኖ በቀረ ነበር፡፡ ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም አዳዲስ የደስታ ምንጮችን በማግኘት፣ ስለ እግዚአብሔር ጥበብ ፍቅርና ኃይል እያደር የበለጠ ግልጽ የሚሆን ዕውቀት እያገኘ በመጣ ነበር፡፡ ከጊዜ ወደጊዜም የተፈጠረበትን ዓላማ ይበልጥ እያሟላ በመጣ ነበር፡፡ የፈጣሪውን ክብርም የበለጠ እያንፀባረቀ በሄደ ነበር፡፡EDA 10.2

    ነገር ግን ይህ ሁሉ ዕድል ትዕዛዝ ባለማክበር ምክንያት ተሰናከለ፡፡ በኃጢአት ምክንያት መለኮታዊ ተምሳሌነቱ ተጐሳቆለ፡፡ ጭራሽ ከነመልኩም ሊጠፋ ምንም አልቀረውም ነበር፡፡ የሰው አካላዊ አቅሙ ደከመ፣ የአዕምሮው ችሎታም ቀነሰ፡፡ መንፈሳዊ የማየት ችሎታውም ፈዘዘ፡፡ የሞት ተገዥም ሆነ፡፡ ይሁንና የሰው ዘር ተስፋየለሽ ሆኖ ይቀር ዘንድ እግዚአብሔር አልተወውም፡፡ ወሰን በሌለው ፍቅርና ምህረት የመዳን ዕቅድ ተቀየሰ፣ የሽግግር ሕይወትም ታቀደ፡፡ በሰው ልጅ ውስጥ የፈጣሪው ተምሳሌት እንደተጠበቀ እንዲቆይ ፣ ሊፈጠር ወደነበረበት ፍፁማዊ ደረጃ እንዲመለስ ፣ የአካሉ፣ የአዕምሮውና መንፈሳዊ ዕድገቱ እንዲለመልምና እግዚአብሔር ሰውን የፈጠረበት መለኮታዊ ዓላማ ይታወቅ ዘንድ መደረግ የነበረበት የማዳን ሥራ ይኸው ብቻ ነበር፡፡ የትምህርት ዋና ዓላማና የሕይወት ታላቁ ግብም ይኸው ነበር፡፡EDA 11.1

    የፍጥረትና የመዳን መሠረት የሆነው «ፍቅር» የእውነተኛው ትምህርትም መሠረት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለሕይወት መሠረት እንዲሆን እግዚአብሔር በሰጠው ትዕዛዝ ውስጥ በግልጽ ተመልክቷል፡፡ የመጀመሪያውና ታላቁ ትዕዛዝ «እግዚአብሔር አምላክህን በፍፁም ልብህ፣ በፍፁም ነፍስህ በፍፁም ኃይልህ በፍፁም ሐሳብህ ውደድ፡፡» (ሉቃ 10፡22) የሚል ነው፡፡ ወሰን የሌለበትን ታላቅ አምላክ በፍፁም ኃይል በፍፁም ሀሳብና በፍፁም ልቦና ማፍቀር ማለት የሁሉንም ክፍለ አካላት ሙሉ ኃይል ማዳበር ማለት ነው፡፡ ይህ ደግሞ በሁለንተናችን የእግዚአብሔር ተምሳሌነታችን ወደቀድሞው ደረጃው ተመለሰልን ማለት ነው፡፡EDA 11.2

    እንደ መጀመሪያው ሁሉ ሁለተኛው ትዕዛዝም «ሰውን ሁሉ እንደራስህ ውደድ፡፡» የሚለው ነው፡፡ (ማቴ 22፡39)፡፡ የፍቅር ሕግ አካላችን አዕምሮአችንና ነፍሳችን ለእግዚአብሔርና ለወገኖቻችን አገልግሎት እንዲውል ማድረግን ይጠይቃል፡፡ ይህ አገልግሎታችን ደግሞ ለሌሎች በረከት እንድንሆን ሲያደርገን ለራሳችንም እጅግ በጣም ብዙ ሲሳይ ያመጣልናል፡፡ ራስን አለመውደድ የእውነተኛ ዕድገት ሁሉ መሠረት ነው፡፡ ራስ ወዳድ ባልሆነ መንገድ ስናገለግል ልዩ ልዩ ተሰጥኦዎቻችንን ሁሉ እጅግ በሚያበለጽግ እውቀት እንባረካለን፡፡ የአምላክ መልክ ተምሳሌነታችን እያደር ይበልጥ እየተሟላ ይመጣል፡፡ የእግዚአብሔርን መንግሥት በልቦናችን ተቀብለናልና ለመንግሥተ ሰማያት ብቁ እንሆናለን፡፡EDA 12.1

    ከዚህ በላይ እንደተመለከትነው የእውነተኛ ዕውቀት ሁሉ መሠረት ስለሆነ የመጀመሪያው የትምህርት ዓላማ እርሱ ራሱን ወደሚገልጥበት አቅጣጫ አዕምሮአችን ማቅናት ነው፡፡ አዳምና ሄዋን ከእግዚአብሔር ጋር በቀጥታ በመገናኘት ዕውቀትን ተቀበሉ፡፡ በድንቅ ሥራዎቹም ስለርሱ ተማሩ፡፡ ፍጹም በነበረው ደረጃቸው መጀመሪያ የተፈጠሩት ነገሮች ሁሉ የእግዚአብሔር ሀሳብ መግለጫዎች ነበሩ፡፡ ለአዳምና ሄዋን ተፈጥሮ ራሷ በመለኮታዊ ጥበብ የተሞላች ነበረች፡፡ ነገር ግን የሰው ልጅ ሕግን በመተላለፉ ምክንያት በቀጥታ ግንኙነት ይበልጡንም በድንቅ ሥራዎቹ አማካይነት ስለእግዚአብሔር ማንነት ያገኝ የነበረው ትምህርት ተቋረጠበት፡፡ መሬት በኃጢአት ስለተበከለች የፈጣሪን ክብርና ሞገስ በደበዘዘ ሁኔታ ማንፀባረቅ ጀመረች፡፡ በእርግጥ የርሱ የማስተማሪያ መሣሪያዎች ፈጽመው አልጠፉም፡፡ በእርሱ ታላቅ የፈጠራ ሥራ በሆኑት ነገሮች በእያንዳንዱ ገጽ ላይ የእርሱ የእጅ ጽሁፍ አሁንም ይነበባል፡፡ ተፈጥሮ ስለፈጣሪዋ አሁንም ትናገራለች፡፡ ይሁንና እነኝህ መገለጫዎች ሁሉ ያልተሟሉና ጥራት የሚጐድላቸው ናቸው፡፡ በዚህ በወደቅንበት ደረጃ ላይ እያለን በደከመ ጉልበታችንና እንዲህ ውስን በሆነ የማየት ችሎታችን መግለጫዎቹን በትክክል ተርጉመን መረዳት ያዳግተናል፡፡ እግዚአብሔር ጽፎ ከሰጠን ቃሉ በተጨማሪ ስለርሱ የተሟላ መግለጫ ያስፈልገናል፡፡EDA 12.2

    ቅዱስ መጽሐፍት የእውነት ትክክለኛ መመዘኛዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም በትምህርት ዓለም ውስጥ ከፍተኛ ቦታ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ለእርሱ ስም የሚመጥን ትምህርት ለማግኘት ፈጣሪ ስለሆነው እግዚአብሔርና አዳኝ ስለሆነው ክርስቶስ በቅዱስ ቃሉ ውስጥ የተገለጠውን ዕውቀት ማግኘት አለብን፡፡EDA 13.1

    እያንዳንዱ በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ሰው ከፈጣሪው ባሕሪ ጋር የተዛመደ ግለሰባዊ የማሰብና የመሥራት ኃይል ታድሎታል፡፡ ይህ ኃይል በውስጣቸው ያደረባቸው ሰዎች፤ ኃላፊነትን መሸከም የሚችሉ የመሥሪያቤት መሪዎችና አርአያነት ያላቸው ተግባቢ ሰዎች ይሆናሉ፡፡ ወጣቶች የሌሎች ሰዎችን አስተሳሰብ የሚያንፀባርቁ ብቻ ሳይሆኑ የራሳቸው የመጠቀ አስተሳሰብ ያላቸው እንዲሆኑ አድርጐ ማሰልጠንና ይህ ኃይል በውስጥ እንዲዳብር ማድረግ የእውነተኛ ትምህርት ተግባር ነው፡፡ ጥናታቸው ሰዎች በተናገሩትና በፃፉት ሐሳብ ዙሪያ ተከልሎ ከመወሰን ይልቅ፣ ተማሪዎች የዕውነት ሁሉ ምንጭ ወደሆነው፣ በተፈጥሮና በመገለጥ ለምርምር በሰፊው ወደተከፈተው መስክ ሊያመሩ ይገባል፡፡ በተግባርና በዓላማ ታላላቅ መረጃዎች ላይ ቢያተኩሩ አእምሮአቸው ይሰፋል ፣ ጥንካሬም ያገኛል፡፡ ተምሮ እንዳልተማሩ እንዳይሆኑ የትምህርት ተቋሞች ጠንካራ የአስተሳሰብና የተግባር ሰዎችን፣ ለአንዳንድ ሁኔታዎች የሚገዙ ባሪያዎች ሳይሆኑ ጌቶች የሚሆኑና ሰፊ አእምሮና ንፁህ አስተሳሰብ ያላቸው፣ በሚያምኑባቸው ጉዳዮች ላይም ድፍረት የሚኖራቸው ወጣቶችን ማፍራት አለባቸው፡፡EDA 13.2

    እንዲህ ዓይነቱ ትምህርት አእምሮን ሥነ ሥርዓት ከማስተማርና የአካል ቅልጥፍና ሥልጠና ከመውሰድ የበለጠ ትምህርት ይሰጣል፡፡ እውነትና ትክክለኛነት በራስ መውደድ ስሜት ወይም ዓለማዊ ምኞት በከንቱ እንዳየለወጡ መንፈሳችንን ያጠነክረዋል፡፡ አዕምሮአችን ክፉውን መዋጋት ይችል ዘንድ ጥሩ ምሽግ ይሆንለታል፡፡ ጥልቅ በሆነ ስሜት ተነሳስቶ ወደጥፋት ከማዘንበል ይልቅ እያንዳንዱ እንቅስቃሴና ፍላጐታችን ከታላላቅ የጽድቅ መሠረታዊ ሐሳቦች ጋር እንዲስማሙ ያደርጋል፡፡ የርሱ ፍፁም የሆነ ባህሪይ ባረፈብን ጊዜ አእምሮአችን ይታደሳል፣ ነፍሳችንም በእግዚአብሔር ተምሳሌነት ትቀረፃለች፡፡ ከዚህ የላቀ ምን ዓይነት ትምህርት ሊኖር ይችላል? በዋጋ የሚስተካከለውስ ምን ነገር ይገኛል?EDA 14.1

    «ጥበብ ……… በምዝምዝ ወርቅ አትገመትም፡፡ ብርም
    ስለዋጋዋ አይመዘንም፡፡ በኦፊር ወርቅ በከበረ መርግድና
    በስንፔር አትገመትም፡፡ ወርቅና ብርጭቆ
    አይወዳደሯትም፡፡ በጥሩ ወርቅም ዕቃ አትለወጥም፡፡
    ስለዛጐልና ስለአልማዝ አይነገርም፡፡ የጥበብ ዋጋ ከቀይ
    ዕንቁ ይልቅ ይበልጣል፡፡» ኢዮብ 28፡15-18፡፡
    EDA 14.2

    እግዚአብሔር ለልጆቹ ያሰበላቸው በሰው ልጅ አስተሳሰብ ሊደረስበት የማይችል እጅግ በጣም ከፍ ያለ ነገር ነው፡፡ ሊደረስበት የሚገባ ዋናው ግብ እግዚአብሔርን ማምለክና እግዚአብሔርን መምሰል ነው፡፡ ለተማሪው እፊቱ የማያቋርጥ የዕድገት ጐዳና ተከፍቶለታል፡፡ ሊደርስበት የሚገባው አንድ ግብ አለ፡፡ መልካም ንፁህና ክቡር የሆነውን ሁሉ የሚያጠቃልል አንድ የስኬት ደረጃም አለው፡፡ በሁሉም የእውነተኛ ዕውቀት ዘርፎች ሁሉ እጅግ በፍጥነት መምጠቅ ይችላል፡፡ ሰማያት ከመሬት የሚርቁትን ያህል ከግላዊና ጊዜያዊ ፍላጐቶች እጅ በራቀ ሁኔታ ጥረቶቹ ሁሉ ወደ ከፍተኛ ግብ ያመራሉ፡፡EDA 14.3

    ስለ እግዚአብሔር ያለውን ዕውቀት ለወጣቱ ትውልድ በማካፈልና የልጁን ፀባይ ከእግዚአብሔር ባህሪይ ጋር የሚያዋህድና ከመለኮት ሐሳብ ጋር የሚስማማ ሰው በከፍተኛና ክቡር ተግባር ፈፀመ ማለት ነው፡፡ ወደ እግዚአብሔር ክቡር ዓላማ ለመድረስ ፍላጐቱን ባነቃቃ መጠን እንደሰማይ የራቀና እንደ ዩኒቬርስ የሰፋ ትምህርት ማዘከር ይችላል፡፡ በዚህ ምድር በሚኖረን ሕይወት የማያልቅና በመጭውም ሕይወት የሚቀጥል፣ ለተዋጣለት ተማሪም የዝግጅት ትምህርት ቤት ከሆነችው ኪዚች ዓለም ተሻግሮ እላይ በሚገኘው የከፍተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ለመግባት የሚያስችለው ይለፍ ያስገኝለታል፡፡EDA 15.1

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents