Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents
የተመረጡ መልእክቶች (ሁለተኛው መጽሐፍ) - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First

    የእግዚአብሔርን ሰራዊት የሚከዱ ሰዎች

    ወንድም ኤክስ በቢሮ ውስጥ ከእግዚአብሔር ሥራ ጋር ባለው ግንኙነት ሲያገለግል ሳለ ያደርገዋል ብዬ የፈራሁትን ያንኑ ነገር ነው ያደረገው፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ሥራ ስለሆነ ሙሉ ልቡን በሥራው ላይ በማድረግና ከእርሱ በፊት የነበሩት እንዳደረጉት ሁሉ ሀላፊነቶቹንና ሸክሞቹን በመሸከም በተመደበበት ቦታ ለእግዚአብሔር ፈቃድ በመታዘዝ ራሱን ክዶ ቢሆን ኖሮ በንግድ ሥራ የሚያገኘውን ያህል የገንዘብ ጥቅም ባያገኝም ከጊዜ ጋር ተለዋዋጭ አለመሆኑን ያሳይ ነበር፡፡ ነገር ግን ደስ ሲለውና ለእርሱ መስሎ በታየው ጊዜ ቢሮውን ለቆ የሚወጣ ከሆነ ለቢሮው ያለው ፍላጎት ምን ያህል ትልቅ ነው? በክርስቶስ አመራር ሥር ያሉ ወታደሮች እንዲህ ማድረግ አለባቸውን? በአገር መከላከያ ሰራዊት ውስጥ ያሉ ወታደሮች ይህን ቢያደርጉ ኖሮ እንደ ከሃዲዎች የሚቆጠሩ እስከሆነ ድረስ በክርስቶስ ሰራዊት ውስጥ ያሉትን እንደ እነዚህ ያሉ ወታደሮችን የሰማይ ዩኒቨርስ እንዴት ይመለከታቸው ይሆን? የእግዚአብሔርን ሥራ ቅዱስነት በማድነቅ በሥራው ላይ የሚሰማራ ማንም ቢሆን፣ የሚያገኘው ዓለማዊ ጥቅም ምንም ቢሆን፣ ያንን ለማግኘት ሲል ከሥራው ወደ ኋላ አያፈገፍግም፡፡ Amh2SM 213.2

    ወንድም ዋይ ሆይ፣ እግዚአብሔር ለአንተና ለወንድም ኤክስ እጅግ ምህረቱን አብዝቶላችኋል፡፡ በሁለታችሁም ዘንድ አደጋ የተጋረጠበትን ሕይወት እርሱ በጸጋው አድኗል፡፡ ባሕርይን እንድትገነቡ ጥሩ አጋጣሚዎችን በማምጣት ቀናት፣ ወራትና ዓመታት ተሰጥተዋችኋል፡፡ በክርስቶስ መንፈስ መሞላት እንድትችሉ እግዚአብሔር ከሥራው ጋር አገናኝቶአችኋል፡፡ እያንዳንዱ ቀን፣ እያንዳንዱ ሰዓት ወደ እናንተ የሚመጣው የራሳችሁን ደህንነት እንድትፈጽሙ ብቻ ሳይሆን ነፍሳትን ወደ ክርስቶስ በማምጣት፣ የእርሱን መንግሥት በመገንባት፣ እና የእግዚአብሔርን ክብር በመግለጥ ወኪሎች እንድትሆኑ በደም እንደተገዛ እድል ሆኖ ነው፡፡ እግዚአብሔር ለሥራው ጥንካሬና መሰጠት እንዲኖር ይጠራል፡፡ በእርግጥ ከእግዚአብሔር ጋር አብረው ሰራተኞች የሆኑት የሥራውን ሸክም በመሸከም፣ እርሱ እንደሚልከው አገልጋይ፣ «በተሰጠኝ ሀላፊነት ታማኝ ሆኜ ካልቆምኩ ወዮልኝ» የሚል ስሜት ይሰማቸዋል፡፡ Amh2SM 214.1

    ወንድሜ ሆይ፣ ለሥራው ያለህ የልብ ፍላጎት ሥራውን እንዲህ በቀላሉ እንደምትጥል ከታየው እውነታ ያልተሻለ ከሆነ ምንም የምለው ነገር የለኝም፣ በቢሮህ እንድትቆይ ወይም ወንድም ኤክስን ወደ ስራው ለመመለስ የማቀርበው ተማጽኖ የለኝም፡፡ ሁለታችሁ እያሳያችሁ ያላችሁት እምነት ሊጣልባችሁ የማትችሉ ሰዎች መሆናችሁን ነው፡፡ በሥራው ላይ እንድትቆዩ የሚሰጡአችሁ ተጨማሪ ማባበያዎች ለእግዚአብሔር የሚያስደስቱ አይደሉም፡፡ Amh2SM 214.2

    እናንተ ከመልቀቃችሁ የተነሳ ሥራው ለጊዜው አለመመቻት የሚገጥመው ቢሆንም ለአንድ አፍታም ቢሆን ለእናንተም ሆነ ለማንኛውም ሌላ ሰው የዶላሮችና የሳንቲሞች ጉቦ አልሰጥም፡፡ ክርስቶስ በላይ ሆኖ ይቆጣጠራል፡፡ የእርሱ መንፈስ ማንኛውንም ነገር እንድታደርጉ ወይም ለእውነት ብላችሁ ማንኛውንም ነገር ለማድረግ ፈቃደኛ እንድትሆኑ የማያደርጋችሁ ከሆነ ያንን ትምህርት መማር የምትችሉት በፈተና ውስጥ በማለፍ ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሔር የእያንዳንዱን ነፍስ እምነት ይፈትናል፡፡ ክርስቶስ መጨረሻ በሌለው መስዋዕትነት ገዝቶናል፡፡ እርሱ ሀብታም ሆኖ ሳለ እኛ በእርሱ ድህነት የዘላለማዊ ሀብት ባለቤቶች መሆን እንድንችል ለእኛ ሲል ደሃ ሆነ፡፡ ያለን ችሎታና እውቀት ሁሉ ለእርሱ ክብር እንድንጠቀም ጌታ በተውሶ የሰጠን ነገሮች ናቸው፡፡ ፈቃደኞች ከሆንን በክርስቶስ መስዋዕትነት ተካፋዮች መሆን ለእኛ ጥሩ ዕድል ነው፡፡ Amh2SM 214.3

    በዚህ ሥራ ውስጥ የመሪነት ሚና የተጫወቱ፣ ልምድና ቅድስና ያላቸው፣ ራሳቸውን የካዱና ለሥራው ስኬት ማንኛውንም ነገር መስዋዕት ለማድረግ ያላመነቱ ሰዎች፣ አሁን በመቃብር ውስጥ ተኝተዋል፡፡ የመንፈሳዊ ሕይወት መርሆዎች ለቤተ ክርስቲያን የተላለፈባቸው እግዚአብሔር የሾማቸው መተላለፊያ መንገዶች ነበሩ፡፡ ከፍተኛ ዋጋ ያለው ልምድ ነበራቸው፡፡ የማይሸጡና የማይለወጡ ሰዎች ነበሩ፡፡ ንጽህናቸው፣ መሰጠታቸውና ራሳቸውን መስዋዕት ማድረጋቸው፣ ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸው ሕያው ግንኙነት ለሥራው ግንባታ በረከቶች ነበሩ፡፡ ተቋሞቻችን ራስን መስዋዕት በማድረግ መንፈስ ይታወቁ ነበር፡፡ Amh2SM 215.1

    ነገር ግን በአንዳንድ አቅጣጫዎች ሥራው አሽቆልቁሏል፡፡ በመጠንና በመገልገያ መሳሪያዎች በኩል እድገት ቢያሳይም የቅድስና እጥረት ይታያል፡፡ በድህነት ምክንያት እየታገልን በነበርንባቸው ቀናት፣ ሥራውን ለመገንባት እግዚአብሔር እንዴት አስደናቂ በሆነ ሁኔታ እንደሰራ የተመለከቱት ሰዎች፣ ከእግዚአብሔር ጋር ባቆራኛቸው ቅዱስ ቁርኝት ከስራው ፍላጎት ጋር ከመታሰር የበለጠ ክብር ሊሰጣቸው እንደማይችል ተሰምቷቸው ነበር፡፡ ገንዘብን በተመለከተ ሸክማቸውን በመጣል ከእግዚአብሔር ጋር ስምምነት መፍጠር ይችላሉን? አይችሉም፡፡ አመለካከቱን እንደ ጊዜው ሁኔታ የሚለዋውጥ እያንዳንዱ ሰው የተመደበበትን ሥራ ቢተውም እነርሱ ሥራቸውን በፍጹም አይተዉም፡፡ እንዲህ ይላሉ፣ «ጌታ በዚህ ቦታ ካስቀመጠኝ ሥራውን ተቀባይነት ባለው መልክ ለማከናወን በየቀኑ ከእርሱ እየተማርኩ ታማኝ መጋቢ እንድሆን ይሻል፡፡ እግዚአብሔር እስኪለቀኝ ድረስ ባስቀመጠኝ ቦታ እቆማለሁ፡፡ ተግባራዊና ከሙሉ ልብ የሆነ ክርስቲያን ማለት ምን ማለት እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ በመጨረሻ ሽልማቴን እጠብቃለሁ፡፡» Amh2SM 215.2

    በሥራው ቀደምት ታሪክ ውስጥ ሥራውን ለመገንባት መስዋዕትነት የከፈሉ አማኞች በተመሳሳይ መንፈስ የተሞሉ ነበሩ፡፡ ሥራው የተሳካ እንዲሆን እግዚአብሔር ከሥራው ጋር ግንኙነት ካላቸው ሁሉ ያልተቆጠበ የነፍስ፣ የአካልና የመንፈስ፣ የአገልግሎቶቻቸውንና የችሎታዎቻቸውን ቅድስና እንደፈለገ ተሰምቷቸው ነበር፡፡ ከመለኮታዊ ወኪሎች ጋር በመተባበር ኃይሎቻቸውን ሁሉ ለእግዚአብሔር እንዲያውሉ እና እያንዳንዱን የአካል ክፍል በሥራ ላይ በማዋል የተገኘውን ያደገ ችሎታ ለእግዚአብሔር እንዲሰጡ በመጠየቅ ምስክርነቶች መጡላቸው፡፡ Amh2SM 215.3