Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents
የተመረጡ መልእክቶች (ሁለተኛው መጽሐፍ) - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ክፍል 7—የመድኃኒቶች አጠቃቀም

    መግቢያ

    የሰባተኛ ቀን አድቬንቲስቶች ጄኔራል ኮንፍረንስ ከተመሰረተበት ከግንቦት 1863 ዓ.ም በኋላ ብዙም ሳይቆይ፣ ቤተ ክርስቲያን 3,500 አባላት በነበሯት ወቅት፣ ኤለን ጂ ኋይት የመልካም ጤንነትን እና በአካል ጤናና በመንፈሳዊ ልምምድ መካከል ያለውን የቀረበ ግንኙነት እንዲገነዘቡ የአድቬንቲስቶችን ትኩረት የሳበውን ራዕይ ተቀበለች፡፡ የተሰጠው ብርሃን አመጋገብን፣ የንጹህ አየርን ዋጋ፣ የውኃ ጥቅምን፣ ጤናማ አለባበስን፣ የሰውነት እንቅስቃሴን፣ እረፍትን፣ ወዘተ… አካቶ በርካታ የሆኑ የሕይወት ክፍሎችን የነካ ነበር፡፡ በሰኔ 6 ቀን 1863 ዓ.ም የተሰጠውና በዚህ ራዕይ ውስጥ ጎልቶ ይታይ የነበረው ሀኪሞች ምንም ሳይመስላቸው ስለሚያዟቸው ጎጂ ስለሆኑ መድኃኒቶች የተሰጠው ብርሃን ነበር፡፡Amh2SM 276.1

    ቀጥለው በነበሩ አመታት ውስጥ ጤንነትን በጥሩ ሁኔታ መጠበቅንና ለበሽተኞች መጠንቀቅን በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ ለጤና ተቋማት የቀረበ ጥሪና በእነዚህ ተቋማት ውስጥ ሰባተኛ ቀን አድቬንቲስቶች እንዴት መሥራት እንዳለባቸው በተመለከተ ሊመሩአቸው የሚገቡ መርሆዎችና የእነዚህ መርሆዎች አጠቃቀም በዝርዝር በብዙ ራዕዮች መልክ ተሰጥቶ ነበር፡፡Amh2SM 276.2

    በእነዚህ ጉዳዮች ላይ ሚስስ ኋይት ብዙ ጽፋለች፡፡ የመጀመሪያው አጠቃላይ መልእክት የወጣው በ1864 ዓ.ም በታተመው እስፕሪቹዋል ጊፍትስ በሚል መጽሐፍ ቅጽ 4 ገጽ ከ120 እስከ 151 ላይ «ጤና” የሚል ርዕስ በተሰጠው ጽሁፍ ውስጥ ነበር፡፡ ከዚያም ሚስስ ኋይት ይህንን 30 ገጽ የነበረውን ጽሁፍ «በሽታና መንስኤዎቹ» በሚል አጠቃላይ ርዕስ ሥር ወደ ስድስት የሚሆኑ የተለያዩ ጽሁፎችን አስፋፍታ ለሕትመት አቅርባለች፡፡ በ1865 ዓ.ም እነዚህ ጽሁፎች በኤልደር እና ሚስስ ኋይት ተሰባስበው «ጤና ወይም እንዴት መኖር እንዳለብን» በሚል ርዕስ ቁጥር በተሰጣቸው ስድስት መጽሔቶች ውስጥ ተካተዋል፡፡ በእያንዳንዱ ቁጥር ውስጥ አንድ የኤለን ጂ ኋይት ጽሁፍ ቀርቦ ነበር፡፡ ቀጥለው በነበሩት በርካታ አመታት ውስጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ የኃይማኖት ድርጅቱ ጥናታዊ መጽሔቶች በጤና ርዕስ ላይ ሚስስ ኋይት የጻፈቻቸውን ጽሁፎች ይዘው ነበር፡፡ በ1890 ዓ.ም ክርስቲያን ቴምፔራንስ ኤንድ ባይብል ሃይጂን በሚል መጽሐፍ በመጀመሪያው አጋማሽ ላይ የጤና መልእክትን አጠቃላይ ስዕል አቅርባለች፡፡ በ1905 ዓ.ም በዚህ ርዕስ ላይ የሥራዋ ቁንጮ የሆነውን ዘ ሚኒስትሪ ኦቭ ሂሊንግ የሚለውን መጽሐፍ አሳተመች፡፡ ይህን መጽሐፍ ያሳተመችው በአሜሪካና ከአሜሪካ ውጭ ባሉ አገሮች በሰፊው እንዲሰራጭ አቅዳ ነበር፡፡Amh2SM 276.3

    ሚስስ ኋይት በጤና ላይ ባቀረበቻቸው አጠቃላይ መልእክቶች በእያንዳንዱ ውስጥ ስለ መርዘኛ መድኃኒቶችና በሽተኞችን ለማከም ያላቸውን ጠቀሜታ አንስታለች፡፡ መጀመሪያ በተሰጠው የጤና ተሃድሶ ውስጥ ጎልቶ የሚታየው ይህኛው ክፍል አስቀድማ ባቀረበችው ባለ ሰለሣ ስምንት ገጽ እስፕሪቹዋል ግፍትስ በሚል መልእክት ውስጥ የመጀመሪያዎቹን ስምንት ገጾች ሸፍኗል፡፡ «በሽታዎችና መንስኤዎቹ» በሚል ርዕስ ሥር ከቀረቡት መልእክቶች ውስጥ ስለ መድኃኒቶች ለመጻፍ አንድ ሙሉ ምዕራፍን ጥቅም ላይ አውላለች፡፡Amh2SM 277.1

    በጊዜው የኤለን ኋይት ድምጽ ብቻውን አልነበረም፡፡ በአትላንቲክ በሁለቱም ወገኖች በቂ ምርመራ አለመኖሩን የተቃወሙና በተለምዶ የሚታዘዙ መርዘኛ መድኃኒቶችን መጠቀምን በተመለከተ አጠንክረው ጥያቄ ያነሱ የነበሩ አንዳንድ ሐኪሞች ነበሩ፡፡ ከዚህ የተነሳ በሽተኞችን ለማከም የመድኃኒት አጠቃቀምን በተመለከተ ቀስ በቀስ ለውጥ መጣ፡፡ ዘመናዊ የሕክምና ትምህርት ከሳይንሳዊና በቤተ ሙከራዎች ውስጥ ከሚደረግ ሙከራ ጋር አብሮ ካደገበት የ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የመጀመሪያዎቹን አሥር አመታት ተከትለው በነበሩት አመታት ውስጥ እነዚህ ለውጦች እጅግ ፈጣንና አስደናቂ ነበሩ፡፡Amh2SM 277.2

    ሚስስ ኋይት በቀደምት ጽሁፎቿ ውስጥ በተለየ ሁኔታ በጊዜው ስለነበሩ ሐኪሞችና ስለ መድኃኒቶች አጠቃቀም ጠንከር ያሉ አረፍተ ነገሮችን ተናግራ ነበር፡፡ እነዚህን ነገሮች በትክክል መገምገም እንድንችል፣ አረፍተ ነገሮቹ በተነገሩበት ወቅት ስለነበሩት የሕክምና ልምምዶች የሆነ ነገር ማወቅ አለብን፡፡ የዚህ ዓይነት እውቀት የሚገኘው የዚያን ዘመን የሕክምና ሥነ-ጽሁፍ በመመርመርና አሁን ያለውን በዲ ኢ ሮብንሰን የተጻፈውን የጤና መልዕክታችን ታሪክ የሚለውን መጽሐፍ ከገጽ 13 እስከ 27 በማንበብ ይሆናል፡፡ Amh2SM 277.3

    ሚስስ ኋይት በተለየ ሁኔታ ስለ ቤተ ክርስቲያን እና ስለ አባላቱ ችግሮችና ሥራ በሚገልጹ መጽሐፎቿ ውስጥ ከማንኛውም አንድ ብቸኛ ርዕስ ይልቅ ስለ ጤና ጉዳይና ለሕመምተኞች ስለመጠንቀቅ ብዙ ቦታ ሰጥታለች፡፡ እነዚህ ምክሮች ከሁለት ሺህ በላይ በሆኑ ገጾች በተለያዩ መጸሕፍት ውስጥ ለአጠቃላይ ሕዝብ ቀርበዋል፡፡ መጽሐፍቶቹ የፈውስ አገልግሎት፣ የሕክምና አገልግሎት፣ ምክር በምግብና በአመጋገብ ላይ፣ በጤና ላይ የተሰጡ ምክሮች፣ እና መሻትን መግዛት የሚሉ ሲሆኑ የቤተክርስቲያን ምክሮች በሚለው መጽሐፍ ውስጥ የተካተቱ ጽሁፎችም ይገኛሉ፡፡ ስለ ጤና ተሃድሶ የተሟላ እና የተመጣጠነ እይታ እንዲኖረው አንባቢው ወደ እነዚህ ምንጮች ተመርቷል፡፡Amh2SM 277.4

    በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ከታተሙትና ካልታተሙት ከተለያዩ ምንጮች አራት ምዕራፎችን የመሰረቱ ጽሁፎች ተሰባስበዋል፡፡ እነዚህ ነገሮች በዋነኛነት የተጻፉት ከተቋሞቻችን ጋር በተገናኘ ሁኔታ ለሕክምና ባለሙያዎች ነበር፡፡ ይህ ደግሞ ሚስስ ኋይት ራሷ በራዕይ የተገለጹ መርሆዎችን እንዴት በሥራ ላይ እንዳዋለች ያሳያል፡፡Amh2SM 277.5

    ለበሽተኞች ስለመጠንቀቅ በተናገረቻቸው የተለያዩ ንግግሮቿ ለመድረስ ጥረት ማድረግ ያለብንን ሁኔታ አስቀምጣልናለች፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ በተጠቀመቻቸው ቃሎች እንደታየው ልዩ በሆኑ ሁኔታዎች ውስጥ መድኃኒቶችን፣ መርዘኛ የሆኑትን እንኳን ቢሆን፣ መጠቀም ተገቢና አስፈላጊ የሚሆንባቸው ጊዜያቶችና ሁኔታዎች መኖራቸውን ተገንዝባለች፡፡Amh2SM 278.1

    ቀዶ ጥገና በሚሰጥባቸው ክፍሎች ውስጥ የተቀደሱ ክርስቲያን ሐኪሞች ቀዶ ጥገና በሚያደርጉበት ጊዜ እነርሱን ለመከታተልና ለመምራት ክርስቶስና መላእክቱ በእነዚያ ክፍሎች ውስጥ እንደሚገኙ ማረጋገጫ መስጠቷ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ትልቅ ቀዶ ጥገና ከመደረጉ በፊት መላው ሰውነት ሙሉ በሙሉ ምንም ነገር እስከማያውቅ እና ምንም ነገር እስከማይሰማው ድረስ ኃይለኛ በሆኑ፣ ማለትም ጎጂ በሆኑ መድኃኒቶች ይሞላል፡፡ ቀዶ ጥገናው ከተጠናቀቀም በኋላ በሽተኛው ሕመም እንዳይሰማውና ከሕመም የተነሳ ወደ ቀዶ ጥገና ድንጋጤ እንዳይመለስና በአንዳንድ አጋጣሚዎችም እንዳይሞት ለመከላከል ሐኪሙ መድኃኒቶች ያሉባቸውን የሚያስተኙ ክኒኖች ይሰጣል፡፡Amh2SM 278.2

    የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለማወቅና ለመከተል ጥረት እያደረጉ ሳሉ ዛሬም ጥቂት ያልሆኑ የሕክምና ባለሙያዎች አንድ የህክምና ተማሪ የመድኃኒት አጠቃቀምን በተመለከተ በ1893 ዓ.ም. ሚስስ ኋይትን የጠየቀውን ዓይነት ጥያቄ ይጠይቃሉ፡፡ በደብዳቤው ላይ እንዲህ ነበር ያለው፡- Amh2SM 278.3

    «ቴስቲሞኒስ የሚለውንና ሃው ቱ ሊቭ የሚሉትን ትንንሽ መጻሕፍት ስናጠና እንደተረዳነው ከሆነ በሕክምና ሥራችን ውስጥ መድኃኒት መጠቀምን ጌታ በጽኑ እንደሚቃወም እናያለን፡፡ …ሃው ቱ ሊቭ በሚለው መጽሐፍ ውስጥ እንደተጠቀሰው መድኃኒት ምንን እንደሚገልጽ በርካታ ተማሪዎች እርግጠኛ መሆን አልቻሉም፡፡ ይህ ቃል የሚያመለክተው እንደ ሜርኩሪ፣ ስትሪችናይን፣ አርሴኒክ እና እኛ የሕክምና ተማሪዎች መድኃኒት ብለን የምንጠራቸውን ጠንካራ የሆኑ መርዞችን ነውን ወይስ እንደ ፖታሲየም፣ አዮዲን፣ ስኩይለስ፣ ወዘተ.. ያሉትን ቀለል ያሉ መድኃኒቶችንም ያካትታል? ስኬታችን የሚለካው ለእግዚአብሔር ዘዴዎች ስንገዛ መሆኑን እናውቃለን፡፡ ከላይ የተነሱትን ጥያቄዎች የጠየቅኩት ከዚህ የተነሳ ነው፡፡”Amh2SM 278.4

    ከዚህ ቀጥሎ ባለው በምዕራፍ 28 ላይ ያለው የመጀመሪያው ነገር ሚስስ ኋይት ለሕክምናው ተማሪ የሰጠችው መልስ ነው፡፡ Amh2SM 278.5

    የኋይት ባለአደራዎች፡፡

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents