Loading...
Larger font
Smaller font
Copy
Print
Contents
የተመረጡ መልእክቶች (ሁለተኛው መጽሐፍ) - Contents
  • Results
  • Related
  • Featured
No results found for: "".
  • Weighted Relevancy
  • Content Sequence
  • Relevancy
  • Earliest First
  • Latest First
    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents

    ሰንበት ትልቁ አከራካሪ ጉዳይ

    «በምድርም ለሚኖሩ ለሕዝብም ለነገድም ለቋንቋም ለወገንም ሁሉ ይሰብክ ዘንድ የዘላለም ወንጌል ያለው ሌላ መልአክ ከሰማይ መካከል ሲበር አየሁ፤ በታላቅ ድምጽም፡- የፍርዱ ሰዓት ደርሷልና እግዚአብሔርን ፍሩ ክብርንም ስጡት፤ ሰማይንና ምድርንም ባሕርንም የውኃውንም ምንጮች ለሠራው ስገዱለት አለ» (ራዕይ 14፡ 6-7)፡፡ {2SM 105.2}Amh2SM 105.2

    ይህ መልእክት፣ በደንብ ከተሰማ፣ የእያንዳንዱን ሕዝብ፣ ነገድ፣ ቋንቋና ወገን ትኩረት ቃሉን በጥልቅ ወደ መመርመር ይጠራል፣ የሰባተኛ ቀን ሰንበትን ወደ ውሸት ሰንበት የለወጠውን ኃይል በተመለከተም ትክክለኛ መረዳት እንዲኖር ያደርጋል፡፡ ብቸኛው እውነተኛ እግዚአብሔር ተትቷል፣ ሕጉ ተጥሏል፣ ቅዱስ የሆነው የሰንበት ተቋም በኃጢአት ሰው በአቧራ ውስጥ ተጥሎ ተረግጧል፡፡ ግልጽ የሆነው አራተኛው ትዕዛዝ ችላ ተብሏል፡፡ የሰማያትና የምድር ፈጣሪ የሆነው ሕያው እግዚአብሔር ማን እንደሆነ የሚናገረው የሰንበት መታሰቢያ ተሽሮ በእሱ ፋንታ የሀሰት ሰንበት ለዓለም ተሰጥቷል፡፡ ከዚህ የተነሳ የእግዚአብሔር ሕግ ተጥሷል፡፡ ሀሰተኛው ሰንበት እውነተኛ መስፈርት መሆን አይችልም፡፡ {2SM 105.3}Amh2SM 105.3

    በመጀመሪያው መልአክ መልእክት ሰዎች ዓለምንና በውስጡ ያሉትን ነገሮች ሁሉ የሰራውን፣ ፈጣሪያችንን እግዚአብሔርን እንዲያመልኩ ተጠርተዋል፡፡ ሰዎች የእግዚአብሔርን ሕግ ኃይል የለሽ በማድረግ ለጳጳሳዊው ተቋም አክብሮታቸውን ገልጸዋል፣ ነገር ግን በዚህ ጉዳይ ላይ እውቀት ይጨምራል፡፡ {2SM 106.1}Amh2SM 106.1

    በሰማይ መካከል ይበር በነበረው መልአክ ይሰበክ የነበረው መልእክት ዘላለማዊው ወንጌል ነው፤ ይህ ወንጌል እግዚአብሔር በኤድን ገነት ውስጥ ለእባቢቱ «በሴቲቱና በአንተ መካከል፣ በዘርዋና በዘርህ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ፤ እርሱ ራስህን ይቀጠቅጣል፣ አንተ ሰኮናውን ትቀጠቅጣለህ” (ዘፍ. 3፡ 15) ብሎ ያወጀው ያው ወንጌል ነው፡፡ በጦር ሜዳ ላይ ቆሞ የሰይጣንን ኃይል በመግጠም ስለሚያሸንፈው አዳኝ የመጀመሪያ ተስፋ የተሰጠው እዚህ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ሕግ የባሕርዩ መግለጫ ስለሆነ ክርስቶስ ወደ ዓለማችን የመጣው በቅዱስ ሕጉ ውስጥ እንደተገለጸው የእግዚአብሔርን ባሕርይ ለማሳየት ነበር፡፡ ክርስቶስ ሕግና ወንጌል ነው፡፡ የዘላለሙን ወንጌል የሚያውጀው መልአክ የሚያውጀው የእግዚአብሔርን ሕግ ነው፤ የድነት ወንጌል የሰዎች ባሕርይ በመለኮታዊ ምሳሌ ወደሚሰራበት ሕግን ወደ መታዘዝ ያመጣቸዋል፡፡ {2SM 106.2}Amh2SM 106.2

    በኢሳይያስ ምዕራፍ 58 ላይ የሰማያትና የምድር ፈጣሪ የሆነውን እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ሰዎችን ሥራ ይገልጻል፡- «ከድሮ ዘመን የፈረሱት ስፍራዎች ይሰራሉ፣ የብዙ ትውልድም መሠረት ይታነጻል” (ኢሳ. 58፡ 12)፡፡ የእግዚአብሔር መታሰቢያ፣ የሰባተኛ ቀን ሰንበት፣ ከፍ ከፍ ይላል፡፡ «አንተም፡- ሰባራውን ጠጋኝ፣ የመኖሪያ መንገድንም አዳሽ ትባላለህ፡፡ ፈቃድህን በተቀደሰው ቀኔ ከማድረግ እግርህን ከሰንበት ብትመልስ፣ ሰንበትንም ደስታ፣ እግዚአብሔርም የቀደሰውን ክቡር ብትለው፣ የገዛ መንገድህንም ከማድረግ ፈቃድህንም ከማግኘት ከንቱ ነገርንም ከመናገር ተከልክለህ ብታከብረው፣ በዚያን ጊዜ በእግዚአብሔር ደስ ይልሃል፣ በምድርም ከፍታዎች ላይ አወጣሃለሁ፣ የአባትህንም የያዕቆብን ርስት አበላሃለሁ፤ የእግዚአብሔር አፍ ተናግሯልና» (ኢሳ. 58፡ 12-14)፡፡ {2SM 106.3}Amh2SM 106.3

    በዚህ ቦታ የቤተ ክርስቲያንና የዓለም፣ የታማኞችና የአመጸኞች ታሪክ በግልጽ ተገልጦአል፡፡ ታማኞች በሶስተኛው መልአክ መልእክት እወጃ ሥር ሰማያትንና ምድርን የፈጠረውን እርሱን ለማክበርና ከፍ ከፍ ለማድረግ እግራቸውን ወደ እግዚአብሔር ትዕዛዛት መንገድ መልሰዋል፡፡ ተቃዋሚ ኃይሎች ሕጉን በመጣስ እግዚአብሔርን አለማክበራቸውን አሳይተዋል፣ ከቃሉ የሚወጣው ብርሃን ጳጳሳዊው ሥልጣን በእግዚአብሔር ሕግ ላይ ያመጣውን ጥሰትና እምነትን ለማጥፋት ያደረገውን ጥረት በማሳየት ወደ እርሱ ቅዱስ ሕግጋት ትኩረትን ሲስብ ሰዎች ጠቅላላውን ሕግ ለማጥፋት ሞክረዋል፡፡ ነገር ግን ማጥፋት ይችላሉን? አይችሉም፤ ቅዱሳን መጻሕፍትን በራሳቸው የሚመረምሩ ሰዎች የእግዚአብሔር ሕግ የማይለወጥ፣ ዘላለማዊ ሆኖ የሚኖርና የእርሱ መታሰቢያ የሆነው ሰንበት ከውሸት አማልክቱ ሁሉ ልዩ ወደሆነው ብቸኛው እግዚአብሔር በመጠቆም ለዘላለም ጸንቶ እንደሚኖር ያያሉ፡፡ {2SM 107.1}Amh2SM 107.1

    ሰይጣን የእግዚአብሔርን ሕግ ለመለወጥ በሰማይ የጀመረውን ሥራ ለማከናወን ሳይደክምና ሳይሰለች ጥረት ሲያደርግ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ሕግ ጉድለት ስላለበት መሻሻል ያስፈልገዋል በማለት ከመውደቁ በፊት በሰማይ ያቀረበውን ንድፈ ሀሳብ ዓለም እንዲያምን በማድረግ ተሳክቶለታል፡፡ የክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን ነን ከሚሉት መካከል አብዛኛው ክፍል፣ በቃላቸው ባይሆን እንኳን በአመለካከታቸው፣ ያንኑ ስህተት መቀበላቸውን ያሳያሉ፡፡ ከሕግ አንዲት ነጥብ ወይም ርዕስ ተለውጦ ቢሆን ኖሮ ሰይጣን በሰማይ ማግኘት ያልቻለውን ነገር በምድር ላይ አገኘ ማለት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እና ዓለምን ምርኮኛው ለማድረግ ተስፋ በማድረግ የማታለያ ወጥመዶቹን አዘጋጅቷል፡፡ ነገር ግን ሁሉም በወጥመዱ አይያዙም፡፡ ታዛዥ በሆኑትና ታዛዥ ባልሆኑት፣ ታማኝና እውነተኛ በሆኑት እና ታማኝ ባልሆኑትና ውሸተኞች በሆኑት ልጆች መካከል የመለያ መስመር እየተሳለ ነው፡፡ ሁለት ታላላቅ ቡድኖች ተፈጥረዋል፣ እነርሱም ለአውሬውና ለምስሉ የሚሰግዱ እና እውነተኛውንና ሕያው እግዚአብሔርን የሚያመልኩ ናቸው፡፡ {2SM 107.2}Amh2SM 107.2

    Larger font
    Smaller font
    Copy
    Print
    Contents